Friday, July 20, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል 3



በማቴዎስ 09¸ 06-2 እድን ዘንድ ምን ላድርግ ብሎ ለጠየቀው ኦሪታዊ ባለጸጋ እንኳ የሙሴን ትእዛዝ እንዲጠብቅ አዘዘው፡፡ ፍጹም እንዲሆን ቢፈልግ ርግጥ በትሩፋት ላይ ትሩፋት ለመጨመር ቢፈልግ ሀብቱን ለነዳያን ሰጥቶ እሱን ቢከተለ የሚሻለው መሆኑን አልሰወረም፡፡ እነሱ የሚጠቅሱትን ሙሴም ስለርሱ የጻፈ ስለርሱ የተነበየ መሆኑን ነግሯቸዋል፡፡ በፖለቲካም ለቄሣር ግብር አትስጡ ብሎ ሕዝቡን ያሳምጻል ተብሎ ከመከሰሱ በፊት “ለቄሣር ግብር መስጠት ይገባል ወይስ አይገባም?" ብለው በተንኮል ቢጠይቁት “የመንግሥታችሁን ለመንግሥታችሁ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ስጡ” ብሏቸዋል፡፡
 እንደተገለጠው ለሮማ መንግሥት ግብር የሚሰበስቡ የመንግሥት ተወካዬች በጴጥሮስ በኩል ስለግብር ጉዳይ አንድ ጥያቄ አንሥተው ነበር፡፡ ጥያቄውም “መምህራችሁ ግብር ይከፍላልን” የሚል ነበር፡፡ ጌታም ይህን ጥያቄ ሰምቶ ምንም እንኳ አስገባሪ እንጂ ገባሪ አለመሆኑን ባይደብቃቸውም የነሱን የተንኮል ጥያቄ ባጭሩ ለመቅጨት ወዲያው ከባሕር ዓሣን ከዓሣ የወርቅ እንክብል አስገብሮ እንዲሰጣቸው ተማሪው ጴጥሮስን አዞታል፡፡ 

Friday, July 13, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል 2

ሕዝቡ በጠቅላላ ገበሬውም ሆነ ነጋዴው የመንግሥትም ባለሥልጣን በሚሠራው ሥራ ሁሉ ባለጸጋ ስለነበር የሮም ግዛት ተወዳዳሪ የሌላት ታላቅ አገር ነበረች፤ ታዲያ ምን ያደርጋል እነዚህ ሁሉ ሀብታት ለሕዝቡ ደስታና ውስጣዊ ዕረፍትን ሊያገኙለት አልቻሉም፡፡ ሁልጊዜ በአካባቢው ከሚሰማው የሽብርና የሁከት ድምጽ የተነሳ ባልታሰበ ቀን እንደመስሳለን በሚል ቀቢጸተስፋ ገዝቶት ነበር፤ ያመልኳቸው ከነበሩ ጣዖታትም አንዳችም የተስፋ ድምጽ አልነበረም፡፡ በቀቢጸ ተስፋ ባሕር ውስጥ ገብቶ የሚማቅቀውና መውጣትም የተሳነው አማኛቸውን ሊያረጋጉት አልቻሉም፡፡
ዳዊት እንደተናገረው ዓይን እያላቸው የማያዩ፤ ጆሮ እያላቸው የማይሰሙ፤ እጅ እያላቸው የማይዳስሱ አፍ እያላቸው የማይናገሩ፤ እግር እያላቸው የማይሄዱ ግዑዛን ናቸውና፡፡ ከዚህም የተነሣ ማለት የሚያመልኳቸው ጣዖታት ሊያረጋጓቸውና ሊረዷቸው ስላልቻሉ ሕዝቡ “አማልክቶቻችን የዋሃንና ግድ የለሾች ናቸው” እያሉ በጣዖታቱ ይዘብት ነበር፡፡ የሰው ልጅ ሥልጣኔም በክፋትና በደግነት መካከል የለውን ልዩነት ለማመልከት አልቻለም፡፡ በዚህም አኳኻን ስለ ሰው ልጅ የወደፊት ዕድል ምንም የተስፋ ጭላንጭል አልነበረም፡፡ ሰው በተፈጥሮው ከወዴት መጣሁ? ወዴትስ ነው የምሔደው? ብሎ ራሱን በራሱ የመጠየቅና የመመርመር ስጦታ ያለው ባለአእምሮ ፍጡር ስለሆነ እነዚህ ጥያቄዎች ሁልጊዜ በፊቱ ይደቀኑበታል፡፡ ነገርግን ለነዚህ ጥያቄዎች ከውስጥ ከራሱም ሆነ ከውጭ ከሌላ አጥጋቢ መልስ ስላላገኘ ከላይ እንደገለጥነው የደስታና የኑሮ ጣእሙንና ምሥጢሩን ሊያውቀው አልቻለም፡፡ በሮም ቅኝ ግዛት ውስጥ የሚኖር ሁሉ በዚህ ሁኔታ በቀቢጸ ተስፋ ስለተሞሉ እነሱም ሆነ ሥርዓተ ማኅበራቸው ጠባቂ እንደሌለው መርከብ አቅጣጫው የማይታወቅ ሆነ፡፡ ሕዝቡን ለማስደሰት በሮም የቴያትር ሰገነት ላይ የሚቀርበው የጨዋታ ዓይነትም እንኳ ደም መፍሰስና መደባደብ ስለነበር በጨለማ ላይ የዛፍና የገደል ጥላ ሲጨመር ጨለማው እንደሚጸና ሰቀቀኑን አባብሶት ነበር፡፡

Thursday, July 5, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል 1


ስለ ክርስትና ሃይማኖት ስለ ቤተክርስቲያን በምንናገርበት ጊዜ ሁሉ ትዝ የሚለንና የምናስተውለው የመጀመሪያው ሰው የአዳም ሁኔታ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን እግዚአብሔር የሁላችንን አባት አዳምን በአርአያውና በመልኩ ከፈጠረው በኋላ ባረከው፡፡
ኹሉንም እንዲገዛ ሥልጣን ሰጠው፡፡ በረከቱን ሥልጣኑንና ሲሳዩን ከሰጠው በኋላ ፈጣሪውን የሚያስታውስበት ትእዛዝ አዘዘው፡፡ እሱ ግን በተሳሳተ ምክር ተመርቶ ከፈጣሪው ትእዛዝ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ የሞት ፍርድ ተፈረደበት፡፡ ይህም የሞት ቅጣት ለርሱ ዐቅም ቀላል አልነበረም፡፡ በሱም ብቻ አልቀረም የልጅ ልጆቹ ይህን የሞት ቅጣት በውርስ ተካፈሉት፡፡ የዚህ የሞት ጽዋ ተካፋዮች ሆኑ፡፡ የአዳም ሕግን መተላለፍ የልጆቹም ተባባሪነት በእግዚአብሔርና በነሱ መካከል ያለውን ልዩነት እያሰፋው ሔደ፡፡ የፈጠራቸው እግዚአብሔርን ዘንግተው የሰማይና የምድርን ሠራዊት ማምለክ ጀመሩ፡፡ በጨረቃ፣ በፀሐይና በከዋክብት፣ በእሳት፣ በውኃ፣ በእንስሳትና በአራዊት፣ በዛፍና በተራራ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሰውን ዘር ጨርሶ ለመደምሰስ ስላልፈለገ ይህን የሰው ልጅ መራራና አሰቃቂ ታሪክ ከመጀመሪያው ጀምረው ሲከታተሉ የነበሩ በአንድ አምላክ በማመን የታወቁ ጥቂት ሰዎችን አተረፈ፡፡ እነሱም ከአበው ሄኖክን፣ ኖህን፣ አብርሃምንና ሎጥን ሌሎችንም የመሳሰሉትን ነው፡፡ ከአብርሃም ይስሐቅ፣ ከይስሐቅ ያዕቆብ ተወለደ፡፡ ከያዕቆብም አሥራ ሁለት ልጆች ተወለዱ፡፡ አሥራ ኹለቱን የእሥራኤል ነገድ መሠረቱ፡፡