Showing posts with label ልዩ ልዩ. Show all posts
Showing posts with label ልዩ ልዩ. Show all posts

Sunday, September 14, 2014

ለውጥ በሌለው ሕይወት አቆጣጠር - ዛሬ ስንት ዓመተ ምሕረት ነው ?

አንድ ሶርያዊ ክርስቲያን የሚከተለውን ደብዳቤ በ1983 . ጽፎ ነበር፡፡ ደብዳቤው እንዲህ ይነበባል፡-
«እስከ 1970 . (የተወለደው 1943 . ነው) «በቤተ ክርስቲያን ትምህርት መሠረት ሥጋ ወደሙ እቀበል ነበር፣ አሥራት አወጣ ነበር፣ ገዳማትን ለመርዳት የተቋቋመ ማኅበር አባል ሆኜ ሌት ተቀን እሠራ ነበር፣ ሁል ጊዜ በመንፈሳዊ ሕይወቴ ውስጥ የመለወጥ ስሜት ነበረኝ፣ ለመማር፣ ለመጾምና ለመጸለይ የነበረኝን ትጋት አስታውሰዋለሁ፡፡
ይሁን እንጂ በ1970 ዓ.ም መንፈሳዊ ሕይወቴ ባለበት ቆመ፡፡ እንኳን ከበፊት የተሻለ ምግባር ልፈጽም የነበረኝንም እየተውኩት መጣሁ፡፡ ድካምና መሰልቸት ሕይወቴን ተጫጫነው፡፡ ራዕይ አጣሁ፡፡ ከፊት ለፊቴ ምንም ነገር አይታየኝም፡፡ ግድግዳ ያለ ይመስለኛል፡፡ ቤተክርስቲያን በበለጠ ለማገልገል የነበረኝ ጉጉት ሁሉ ሞተ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በማንኛውም ደብዳቤ ዓመተ ምሕረቱን 1970 እያልኩ እጽፋለሁ፡፡ እስከ አሁን ድረስ (1983 ዓ.ም ማለቴ ነው) በኔ አቆጣጠር 1970 ዓ.ም ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚያ በኋላ በኑሮዬ ውስጥ ምንም የተለወጠ፣ ያደገ ወይም የተስተካከለ ነገር የለምና፡፡ ብፁዕ አባታችን፡- እባክዎ ምክርዎን በመለገስ ወደ 1971 ዓ.ም ያሸጋግሩኝ;»
ሕይወት ካልተለወጠ፣ ካላደገ፣ ሃይማኖት ካልሰፋ፣ ምግባር ካልጸና ፣ ትናንት ያሸነፉንን ኃጢአቶች ዛሬ ካላሸነፍን፣ የደከመውን አበርትተን፣ የተሰበረውን ካልጠገንን፣ ዘመን ተለውጦ ዘመን ቢተካም፣ የምድርን ዕድሜ እንቆጥራለንን እንጂ እኛ እንደሆንን እንደቆምን ነን፡፡
አንዳንዶቻችን ያኔ ሕጻን ሆነን ሥጋ ወደሙ እንደተቀበልን፣ ሌሎቻችን በወጣትነት ለሰንበት ት/ቤትና ለጽዋ መርሐ ግብር በነበረን ትጋት ላይ ሌሎችም በማስተማር፣ ቤተክርስቲያንን በማሰራት፣በማስቀደስ በመጸለይና በመጾም፣ በነበረን የጥንት ምግባር አንዳንዶችም ወደ ምንኩስና (ምናኔ) ሲገቡ በነበራቸው የወጣኒነት ትጋት እዚያው ላይ ዓመተ ምሕረታችን ቆሟል፡፡
አዲስ አበባ አራት ኪሎ መሐል የአርበኞች ኃውልት አለ፡፡ እዚያ ኃውልት ጫፍ ላይ ሰዓት ተሰቅሏል፡፡ ሰዓቱ የሚያመለክተው አርበኞች አዲስ አበባ የገቡበትን ሰዓት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ቆሟል፡፡ የዛሬው ትውልድ ያንን ሰዓት ሲያየው ጀግኖች አባቶቹ ጠላትን ድል አድርገው ሀገሪቱን ነጻ ያወጡበትን ጊዜ ያስብበታል፡፡ ያ ሰዓት የጥንቲቱን ተግባር ብቻ እያመለከተ ቆሟል፡፡ የዛሬውን ትውልድ ጀግንነትና ዝና የሚያሳይ ሰዓት ግን የለም፡፡
 የብዙዎቻችን ሰዓት ቆሟል፡፡ በአንድ ወቅት የሠራነውን መልካም ስራ፣ የነበረን መንፈሳዊ ትጋት፣ የሃይማኖት ጥንካሬና ሰማይ ጥግ የደረሰ ዝና እያመለከተ ቆሟል፡፡ ዛሬ በአቡሻህር አቆጣጠር 2007 ዓ.ም ነው:: በእኛ አቆጣጠርስ ስንት ነው; ያ ሶርያዊ ክርስቲያን «በኔ አቆጣጠር 1970 ዓ.ም ነው» ብሏል፡፡ እርሱ የነበረበትን ዘመን ግን እስከ 1983 ዓ.ም ነበር፡፡
የዘመን መለወጫን በዓል አከበርነውም አላከበርነውም ዘመኑ መለወጡ አይቀሬ ነው፡፡ እያንዳንዷን ቀን ተጠቀምንም አልተጠቀምንም ጊዜው መሮጡ አይቀርም፡፡ እርሱ የራሱን ጊዜ ይቆጥራል፡፡ ይለወጣል፡፡ እኛስ;

 እስቲ ጊዜ ሰጥተን ራሳችንን እንመርምረው፡፡ በሃይማኖት እየጸኑ፣ በምግባር እየበረቱ፣ በትጋት እየጨመሩ፣ በመንፈሳዊ እውቀት እያበሩ፣ ሰማዕትነትን ይበልጥ እያፈኩ ካልሄዱ ዘመኑ ብቻውን ቢቀየር «እንኳን አደረሳችሁ» ያስብላልን;
የአክሱምንም አደባባይ የጎበኘ ሰው ሦስት ነገሮችን መታዘብ ይችላል፡፡ ተጠርቦ ተቀርጾ ሃውልት የሆነ ድንጋይ አለ፡፡ ሃውልት ለመሆን ተጠርቦ ቅርጽ ሳይወጣለት ልሙጥ ሆኖ የቀረ አለ፡፡ ለሀውልትነት ተመርጦ ሳይጠረብ ሳይቀረጽ የቀረ አለ፡፡ በመንፈሳዊ ጉዞም እነዚህ ሦስቱ ነገሮች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡ ለሰማያዊ ዋጋ ተመርጠው በብዙ ፈተና ተጠርበውና ተቀርጸው ጉዞአቸውን የፈጸሙ አሉ፡፡ ተመርጠው ተጠርበው ግን ገና ቅርጽ መያዝ ሲቀራቸው ባሉበት የቀሩ አሉ፡፡ በሌላ በኩል ተመርጠው ከመጡ በኋላ ከዚያ ያለፈ ተግባር ላይ ያልዋሉም አሉ፡፡ የእነዚህ የሦስቱም የዘመን አቆጣጠራቸው ይለያያል፡፡ አንዱ በደረሰበት ዓ.ም ሌሎቹ አልደረሱምና፡፡
በወንጌል ታሪኩ የተጠቀሰው የጠፋው ልጅ አባት ልጁ ከጠፋበት ሀገር ሲመለስ «ይህ ልጄ ሞቶ ነበር ህያው ሆኗል» ብሎ ነበር የተናገረው፡፡ ያ ልጅ እኮ ይንቀሳቀሳል፣ ይበላል፣ ይጠጣል ግን ሞቷል ተባለ ለምን; የሱ የዘመን አቆጣጠር ከአባቱ ቤት ሲጠፋ መቁጠሩን አቁሞ ነበርና፡፡ በመንፈሳዊ ጉዞ የነበረው ለውጥ ስላቆመ ሞተ ተባለ፡፡ ትልቁ ጥያቄ ማን ተለወጠ ነው፡፡ ዘመን ተለወጠ; ሰው ተለወጠ; ወይስ ሁለቱም ተለወጡ; ዘመን ይለወጣል፡፡ አይቀሬ ነው፡፡ የስነ ፍጥረት ስርዓት ሁሉ የእግዚአብሔርን ህግ ሳያፋልስ ይኖራልና፡፡ አስቸጋሪው ነገር እርሱ አይደለም፡፡ እስከ ዘመነ ምጽዓት ዘመን ይመጣል፣ ያልፋል፣ በሌላ ይተካል፡፡ ሰው ተለወጠ; ለሚለው ጥያቄ መልስ ማግኘት ግን ከባድ ነው፡፡ ይህን ጥያቄ ከባድ ያደረገው በሰው ኑሮ ውስጥ ሦስት ዓይነት ለውጥ ስላለ ነው፡፡ በመንፈስ መለወጥ፣ በአካል መለወጥ፣ በባሕላዊም ይሁን በዘመናዊ መንገድ በሚገኝ እውቀት የሰው እውቀት ይለወጣል፣ ያድጋል፣ ይሰፋል፣ ይጎለምሳል፡፡ ወደደም ጠላም የሰው አካል የተፈጥሮውን ሂደት ጠብቆ ይለወጣል፣ ጽንሱ ይወለዳል፣ ሕጻኑ ያድጋል ወጣት ይሆናል፣ ወጣቱ ይጎለምሳል፣ ጎልማሳው ያረጃል፣ አካላዊ ጸባዩም በዚያው ልክ ይለወጣል፡፡
ትልቁ ፈተና መንፈሳዊ ለውጡስ የሚለው ላይ ሲደርስ ነው፡፡ መንፈሳዊ ለውጥ ከነዚህ ከሁለቱ ለውጦች የተለየ ነው፡፡ ተጋድሎ ከሥጋና ደም ጋር አይደለምና፡፡ የሰውየውን ታላቅ ጥረት፣ ሰማዕትነት እና የሃይማኖትን ጽናት የግድ ይላል፡፡ በዚህም የተነሳ በእውቀት ጎልምሰው፣ በዕድሜ አርጅተው፣ በመንፈሳዊ ለውጥ ግን ገና ሕጻናት የሆኑ ወይም ደግሞ በሕጸንነት እድሜ ላይ የጊዜ መቁጠሪያ ሰዓታቸውን ያቆሙ ብዙ ናቸው፡፡
ሌላው ቀርቶ ስለ መንፈሳዊ ሕይወትና ስለ ሃይማኖት እጅግ ብዙ የተማሩ በእውቀት ለሌሎች ሊተርፉ የሚችሉ ሌሎችን አስተምረው ለፍሬ ያበቁ እንŸDን በመንፈሳዊ ሕይወት ለውጣቸው ገና ወጣኒያን ሆነው የሚገኙበት አጋጣሚ አለ፡፡
ስለዚህም ሌላ የዘመን መለወጫ ከማክበራችን. አዲስ አመት ገባ እያልን ዶሮና በግ ከማረዳችን. እንደ ምዕራባውያውኑ ወደ ኋላሩ (Count down) ከመቁጠራችን በፊት ለቀጣዩ ጥያቄ መልስ እንፈልግ፡፡
ለውጥ በሌለው ሕይወት አቆጣጠር - ዛሬ ስንት ዓመተ ምሕረት ነው ?

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


Friday, January 24, 2014

ምሥጢረ ጥምቀት ክፍል-3

ሠ-በማን ስም ልንጠመቅ ይገባል
  ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰዎች የእግዚአብሔርን ልጆች ይሆኑ ዘንድ በሥላሴ ስም ታጠምቃለች፡፡ ይህም ጌታ ራሱ ለሐዋርያቱ ‹‹ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም  ያጠመቃችኋቸው፡፡››  (ማቴ. 28÷19) ብሎ የሰጠውን አምላካዊ ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ደም ከተመሠረተችበት ዘመን አንስቶ በሥላሴ (በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ) ስም መጠመቅ የድኀነት በር ቁልፍ መሆኑን ስታስተምርና ተግባራዊ ስታደርግም ኖራለች፡፡
 ይህንን የወንጌል ቃል የሚያጣምሙ መናፍቃን በኢየሱስ ስም ብቻ መጠመቅ አለብን እንጂ በአብ፣ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ የለብንም ይላሉ፡፡ ለዚህም ማስረጃ አድርገው ለማቅረብ የሚሞክሩት የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስን አነጋገር ነው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ ሃምሳ ከየሃገሩ ለተሰበሰቡት አይሁድ የምሥራቹን ቃል ድምጹን ከፍ አድርጐ ባሰማቸው ጊዜ ልባቸው ተነካ፡፡ ስለዚህም ‹‹ምን እናድርግ›› ብለው ሊያደርጉት የሚገባቸውን እንዲነግራቸው ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹ንስሐ ግቡ፣ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ አላቸው›› (የሐዋ ሥራ 2÷38)፡፡
 2006 ዓ.ም የጥምቀት በዓል አከባበር በጎንደር
ሐዋርያው ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ›› ብሎ ማስተማሩ ለምን ነበር? ለምን ጌታ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁ ያለውን ተከትሎ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠመቁ አላለም? የሚል ጥያቄ ለሚያነሣ ሁሉ ምክንያቱ እንደሚከተለው ነው፡፡በበዓለ ሃምሳ ከየሃገሩ የተሰበሰቡት አይሁድ ከጥንት ጀምሮ በነቢያት አንደበት ይወርዳል ይወለዳል እየተባለ የተነገረለትን መሲሕን ተስፋ ያደርጉ ነበር፡፡ ሐዋርያውም ያ የተስፋው ቃል ዛሬ መፈጸሙንና በተስፋው ቃል መሠረት ከድንግል ማርያም በሥጋ ተወልዶ 33 ዓመተ ከ3 ወር በምድር ላይ ተመላልሦ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ የሰውን ልጅ በደሙ የዋጀው ኢየሱስ ክርስቶስ ትንቢት የተነገረለት ሱባዔ የተቆጠረለት መሆኑን አምነው በሰው ካልተጠመቁ በስተቀር አብርሃም አባታችን እግዚአብሔር አምላካችን በሚለው እምነት ብቻ አምነው ጌታን በሰቀሉት አይሁድ መንገድ የሚጓዙ ከሆነ እንደማይድኑ በመሲሕ አምነው በስሙም ከተጠመቁ ግን እንደ ሚድኑ ሊያስተምራቸው ስለፈለገ የጌታን ስም ለይቶ ጠራ፡፡ በዚህም የጌታን አዳኝነትና መሲሕነት አምነው እንዲቀበሉ በአጽንዖት መናገሩ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ ሳይሆን ሌሎችም ሐዋርያት ከላይ በተጠቀሰው ምክንያት ቤዛ የሆነልንን ጌታ ሰው ሁሉ አምኖ እንዲድን በየሄዱበት የጌታን አዳኝነትና የባሕርይ አምላክነት አሰተምረዋል፡፡ የስብከታቸው ማዕከል የነበረው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡ ምክንያቱም ክህደቱ ጸንቶ የነበረው በጌታ የባሕርይ አምላክነት ላይ ነበርና፡፡ በዚህ የተነሣ የእርሱን አዳኝነትና የባሕርይ አምላክነት ለማሳመን ጌታን የስብከታቸው ማዕከል አደረጉ፡፡

Monday, January 20, 2014

ምሥጢረ ጥምቀት- ክፍል-2

ሐ-የጥምቀት ምሳሌ በብሉይ ኪዳን
1-             ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት የዳኑባት መርከብ የአማናዊቱ ቤተክርስቲያን ምሳሌ መሆንዋ በመጽሐፍ ቅዱስ የተረጋገጠ ነው፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔር በልቡናቸው ያደረው ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት ሲድኑ እግዚአብሔርን ድምፅ ያልሰሙት የኖኀ ዘመን ለአማናዊው ጥምቀት ምሳሌነት እንዳለው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሲገልጽ (ሲያስተምር) #ጥቂቶች ማለትም ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኀ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም፡፡
ፈሪሃ እግዚአብሔር በልቡናቸው ያደረው ኖኀና ቤተሰቡ ከጥፋት ሲድኑ እግዚአብሔርን ድምፅ ያልሰሙት የኖኀ ዘመን ለአማናዊው ጥምቀት ምሳሌነት እንዳለው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሲገልጽ (ሲያስተምር) ‹‹ጥቂቶች ማለትም ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኀ ዘመን በቆየ ጊዜ ቀድሞ አልታዘዙም፡፡ ይህም ውኃ ደግሞ ማለት ጥምቀት ምሳሌው ሆኖ አሁን ያድናል፡፡ የሰውነትን እድፍ ማስወገድ አይደለም ለእግዚአብሔር የበጎ ሕሊና ልመና ነው እንጂ›› 1ጴጥ.3÷20-12፡፡

Wednesday, January 15, 2014

ምሥጢረ ጥምቀት

ክፍል-1
ሀ-አስፈላጊነት

መጠመቅ ማለት መነከር፣ መዘፈቅ፣ ውኃ ውስጥ ገብቶ መውጣት ማለት ነው፡፡ ምሥጢረ ጥምቀት የሥላሴ ልጅነት የሚሰጥበት እና የኃጢአት ሥርየት የሚገኝበት ምሥጢር ነው፡፡
1.      ድኀነትበጥምቀትነው፤
ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን ያልተጠመቀ ሰው አይድንም፡፡ የተጠመቀ ግን እንደሚድን በመዋዕለ ትምህርቱ እዲህ ሲል አስተምራል #ያመነ የተጠመቀም ይድናል$ ማር.16 ቁ 16፡፡ ያመነ ይድናል ብቻ አለማለቱን ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ ጥምቀት ለድኀነት ባያስፈልግ ኖሮ ጌታ ያመነ የተጠመቀም ይድናል ባላለ ነበር፡፡
2. በጥምቀት ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ዳግም እንወለዳለን፤
ኒቆዲሞስ የተባለው የአይሁድ አለቃ በሌሊት ወደ ጌታ ዘንድ ሊማር በሄደ ጊዜ ጌታ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም›› አለው፡፡ ይህ የጌታ ትምህርት ለኒቆዲሞስ ስለረቀቀበትና ስለተቸገረ ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኀፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?›› የሚል ጥያቄ አቅርቦ ነበር፡፡

Friday, July 20, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል 3



በማቴዎስ 09¸ 06-2 እድን ዘንድ ምን ላድርግ ብሎ ለጠየቀው ኦሪታዊ ባለጸጋ እንኳ የሙሴን ትእዛዝ እንዲጠብቅ አዘዘው፡፡ ፍጹም እንዲሆን ቢፈልግ ርግጥ በትሩፋት ላይ ትሩፋት ለመጨመር ቢፈልግ ሀብቱን ለነዳያን ሰጥቶ እሱን ቢከተለ የሚሻለው መሆኑን አልሰወረም፡፡ እነሱ የሚጠቅሱትን ሙሴም ስለርሱ የጻፈ ስለርሱ የተነበየ መሆኑን ነግሯቸዋል፡፡ በፖለቲካም ለቄሣር ግብር አትስጡ ብሎ ሕዝቡን ያሳምጻል ተብሎ ከመከሰሱ በፊት “ለቄሣር ግብር መስጠት ይገባል ወይስ አይገባም?" ብለው በተንኮል ቢጠይቁት “የመንግሥታችሁን ለመንግሥታችሁ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ስጡ” ብሏቸዋል፡፡
 እንደተገለጠው ለሮማ መንግሥት ግብር የሚሰበስቡ የመንግሥት ተወካዬች በጴጥሮስ በኩል ስለግብር ጉዳይ አንድ ጥያቄ አንሥተው ነበር፡፡ ጥያቄውም “መምህራችሁ ግብር ይከፍላልን” የሚል ነበር፡፡ ጌታም ይህን ጥያቄ ሰምቶ ምንም እንኳ አስገባሪ እንጂ ገባሪ አለመሆኑን ባይደብቃቸውም የነሱን የተንኮል ጥያቄ ባጭሩ ለመቅጨት ወዲያው ከባሕር ዓሣን ከዓሣ የወርቅ እንክብል አስገብሮ እንዲሰጣቸው ተማሪው ጴጥሮስን አዞታል፡፡ 

Thursday, July 5, 2012

ቤተክርስቲያን እንዴት ተመሠረተች ? ክፍል 1


ስለ ክርስትና ሃይማኖት ስለ ቤተክርስቲያን በምንናገርበት ጊዜ ሁሉ ትዝ የሚለንና የምናስተውለው የመጀመሪያው ሰው የአዳም ሁኔታ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን እግዚአብሔር የሁላችንን አባት አዳምን በአርአያውና በመልኩ ከፈጠረው በኋላ ባረከው፡፡
ኹሉንም እንዲገዛ ሥልጣን ሰጠው፡፡ በረከቱን ሥልጣኑንና ሲሳዩን ከሰጠው በኋላ ፈጣሪውን የሚያስታውስበት ትእዛዝ አዘዘው፡፡ እሱ ግን በተሳሳተ ምክር ተመርቶ ከፈጣሪው ትእዛዝ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ የሞት ፍርድ ተፈረደበት፡፡ ይህም የሞት ቅጣት ለርሱ ዐቅም ቀላል አልነበረም፡፡ በሱም ብቻ አልቀረም የልጅ ልጆቹ ይህን የሞት ቅጣት በውርስ ተካፈሉት፡፡ የዚህ የሞት ጽዋ ተካፋዮች ሆኑ፡፡ የአዳም ሕግን መተላለፍ የልጆቹም ተባባሪነት በእግዚአብሔርና በነሱ መካከል ያለውን ልዩነት እያሰፋው ሔደ፡፡ የፈጠራቸው እግዚአብሔርን ዘንግተው የሰማይና የምድርን ሠራዊት ማምለክ ጀመሩ፡፡ በጨረቃ፣ በፀሐይና በከዋክብት፣ በእሳት፣ በውኃ፣ በእንስሳትና በአራዊት፣ በዛፍና በተራራ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሰውን ዘር ጨርሶ ለመደምሰስ ስላልፈለገ ይህን የሰው ልጅ መራራና አሰቃቂ ታሪክ ከመጀመሪያው ጀምረው ሲከታተሉ የነበሩ በአንድ አምላክ በማመን የታወቁ ጥቂት ሰዎችን አተረፈ፡፡ እነሱም ከአበው ሄኖክን፣ ኖህን፣ አብርሃምንና ሎጥን ሌሎችንም የመሳሰሉትን ነው፡፡ ከአብርሃም ይስሐቅ፣ ከይስሐቅ ያዕቆብ ተወለደ፡፡ ከያዕቆብም አሥራ ሁለት ልጆች ተወለዱ፡፡ አሥራ ኹለቱን የእሥራኤል ነገድ መሠረቱ፡፡

Friday, June 22, 2012

የጎንደር መንበረ መንግሥት መድኃኔዓለም የአራቱ ጉባኤያት ት/ቤት የጉባዔ ጥሪ

የጎንደር መንበረ መንግሥት መድኃኔዓለም የአራቱ ጉባኤያት /ቤት በአዲስ አበባ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዳራሽ ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሀዲስ በተገኙበት ሰኔ 17 ቀን 2004 .. ታላቅ መንፈሳዊ ጉባዔ አዘጋጅቶላችኋል - ሁላችሁም ተጋብዛችኋል


Wednesday, May 30, 2012

ጰራቅሊጦስ


ቤተ ክርስቲያናችን ከምታከብራቸው ዓበይት በዓላት መካከል አንዱ በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡ ይህ በዓል ጌታችን በሚያርግበት ጊዜ ደቀመዛሙርቱን አንትሙሰ ንበሩ ሀገረ ኢየሩሳሌም እሰከ ትለብሱ ኃይለ እም አርያም ሉቃ 2449 ብሏቸው አርጎ ነበር፡፡ተናግሮ የማያስቀር ነውና ባረገ በ10ኛው በተነሣ በ50ኛው ቀን ጰራቅሊጦስን ሰዶላቸዋል ፡፡



ጰራቅሊጦስ ማለት ፡-
1/ ናዛዚ(አጽናኝ) ማለት ነው ከመንፈስ ቅዱስ ሥራዎች አንዱ ያዘኑትን የተጨነቁትን በተለያየ ነገር ውስጥ ገብተው ግራ የተጋቡትን ሁለ ሰለሚያጽናና ናዛዚ ይባላል ፡፡
2/ከሣቲ (ምስጢር ገላጭ) ማለት ነው የተደበቀውን የሚገልጥ የረቀቀውን የሚያገዝፍ የተሰወረውን የሚያሳይ በመሆኑ ከሣቲ ( ምስጢር ገላጭ) ይባላል ፡፡

Thursday, May 10, 2012

የቅዱሳን መሰወር (ኅብአተ ቅዱሳን) -ክፍል 2



ነቢዩ ኤልያስ
፬. ብሔረ ብፁዓን

ከኻያው ዓለማት ውስጥ የኾነች /ከመሬት ወገን የምትመደብ/ ስውር ምድር ብሔረ ብፁዓን ናት። እንደ ገድለ ዞሲማስ አገላለጽና ሌሎች ቅዱሳት መጻሕፍት፥ በዚህች ቦታ ተሰውረው የሚኖሩ ሰዎች ራሳቸውን ለፈቃደ እግዚአብሔር ያስገዙ ናቸው። በውስጧም ቅዱስ ጋብቻን መፈጸም የሚችሉና ዘርን ለማሰቀረትና ለመተካት ልጅን መውለድ ይችላሉ። ለኃጥአን ያልተፈቀደች የማትገባም ቦታ ናት።

፭. ደብር ቅዱስ

ከምድር ወገን ሆና የተለየች ሥፍራ ናት። አዳም በበደለና ከገነት በወጣ ጊዜ ገነትን በማየት ይጸጸት ዘንድ በዚህች ሥፍራ አኑሮታል። መጽሐፍ ቅዱስ /ብሉይ ኪዳን/ ይህችን ቦታ «ደብር ቀዱስ፣ ከፍ የለች ሥፍራ» በማለት ይጠራታል። /ሄኖክ ፬፥፸፩/። አዳም ከአቤል ሞት በኋላ የተወለደለት ሴት ከነልጆቹ ይኖር እንደ ነበርና በኋላም በኖኅ ዘመን የቃየንን ሴቶች ልጆች በማየት ስተው መውረዳቸውን በዘፍጥረት ትርጓሜ እንረዳለን። «የእግዚአብሔር ልጆችም /በደብር ቅዱስ የሚኖሩ የሴት ልጆች/ የሰውን ሴት ልጆች /የቃየንን ልጆች/ መልካሞች እንደሆኑ አዩ፤ ከመረጧቸውም ሁሉ ሚስቶችን ለራሳቸው ወሰዱ።» /ዘፍ. ፮፥፪/ ይላል።

Friday, May 4, 2012

የቅዱሳን መሰወር (ኅብአተ ቅዱሳን) -ክፍል 1


ዮሐንስ ወንጌላዊ

የሰው ልጆች ወደ እግዚአብሔር በመንፈሳዊ አገልግሎት ባዘነበሉ መጠን ቸርነት የባሕርዩ የሆነ እግዚአብሔር ደግሞ የተለያየ መንፈሳዊ ብቃትን ይሰጣቸዋል፤ ሰማያዊ ምሥጢርን ይገልጥላቸዋል። ቅዱሳን በሥጋቸው በምድር ለጸሎት ቆመው ነፍሳቸው በተመስጦ ገነት መንግሥተ ሰማያት ተነጥቃ ሄዳ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ታመሰግናለች። እንዲሁም በአካል እንደ ነቢያቱ ሄኖክና ኤልያስ በመወሰድ እስከ ጌታችን ዳግም ምጽአት መዳረሻ ቀን በመሰወር እንደሚኖሩ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል።

«መሰወር» የሚለው ቃል የግእዝ ግሱ «ኀብአ»፦ «ሰወረ፥ መሰወር»፤ «ተኀብአ»፦ «ተደበቀ፥ ተሰወረ፥ ራቀ፥ ረቀቀ» ማለት ሲሆን በጥቅሉ ለዓይን እንዳይታይ እንዳይገኝ ሆነ፤ ለምሥጢርም ከሆነ ለአእምሮ ረቀቀ ማለት ነው ።

«መሰወርን» የምንዳስስበት ሃይማኖታዊ ጠገግ ወይም አድማስ በሥጋ ለባሽነት የኖሩትን የሰው ልጆችን በጽድቅና በቅድስና መሰወር የሚያካትት ነው። በዚህም መሠረት ከሰው ልጆች ወገን፦ በቅድስናቸው ብቃት፥ እግዚአብሔር በሰጣቸው ጸጋ እስከ ምጽአት ድረስ በሥጋቸው በብሔረ ሕያዋን እንዲሰወሩ፤ ከሰው ልጆች ዓይን ለጊዜው ለአስፈላጊ ሁኔታ እንዲሰወሩ፤ ከመደበኛ መልካቸው ለጊዜው ሌላ ሰው በመምሰል እንዲሰወሩ፤ መከራ እንዳያገኛቸው የሰወራቸውና ከሞቱ በኋላ ቅዱስ ሥጋቸውን የሰው ልጆች እንዳይቀብሯቸው የተሰወሩት ወዘተ ይገኙባቸዋል።

Sunday, March 18, 2012

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ 3ኛ አረፉ፡፡


የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ማርቆስ መንበር 117 ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ትናንት መጋቢት 8 ቀን 2004 .. አረፉ፡፡ቢቢሲ የግብፅን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ እንደዘገበው ቅዱስነታቸው በካንሰር ሕመም ምክንያት 88 ዓመታቸው አርፈዋል፡፡
በሰሜናዊ ግብፅ፣ አስዩት ውስጥ ሐምሌ 27 ቀን 1915 . ሲወለዱ ናዚር ጋይድ የሚል መጠሪያ ከቤተሰባቸው የተሰጣቸው ቅዱስነታቸው፣  ቅስናን ሲቀበሉ አባ እንጦንስ ተብለው ይጠሩ የነበር ሲሆን አቡነ ሲኖዳ የተባሉት 1955 . የክርስትና ትምህርት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው በተሸሙበት ወቅት ነበር፡፡
ቅዱስነታቸው ካረፉ በኋላ
ቅዱስነታቸው አቡነ ሺኖዳ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 117 ፓትርያርክ ሆነው በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ የተሾሙት ከፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ 6 በኋላ ኅዳር 4 ቀን 1964 . ነበር፡፡

ቅዱስነታቸው ካረፉ በኋላ
ቅዱስነታቸው 5ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የቲዎሎጂ ሴሚናሪ ዲን የሆኑ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሲሆኑ በአገልግሎት ዘመናቸው 3 የአሜሪካን እንዲሁም 1 የጀርመን ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ተቀብለዋል፡፡
ቅዱስነታቸው ሕይወታቸው የትሕርምት፣ የጸሎትና የአገልግሎት እንደነበር የሕይወት ታሪካቸውን የሚዘግቡ ድርሳናት የሚገልጹ ሲሆን ባለፉት 20 ዓመታት የዓለምን ሕዝብ ያስተማሩባቸው 80 መጻሕፍትን ደራሲና የቤተ ክርስቲያኗ ኦፊሴላዊ መጽሔት ኤል-ኬራዛ ዋና አዘጋጅ ነበሩ፡፡