ዮሐንስ ኀፂር ቤተሰቦቹ ያወጡለት ስም ኮሎቦስ የሚል ነው፡፡ በሀገራቸው ቋንቋ አጭር፣
ድንክ ማለት ነው፡፡ በገዳመ አስቄጥስ በተጋድሎ ጸንተው ክብር ካገኙ ቅዱሳን መካከል አንዱና በግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን
ታላቅ ክብር ያለው አባት ነው፡፡ ቤተክርስቲያናችንም ከምትዘክራቸው ቅዱሳን መካከል አንዱ ነው፡፡ /ነሐሴ 29/ ፍልስተ አጽሙን ቤተክርስቲያን ታከብራለች፡፡
አባ ዮሐንስ ኀፂር በላይኛው ግብኝ “ቴባን” በምትባል መንደር በ339 ዓ.ም. ገደማ ተወለደ፡፡ ምንም እንኳን ቤተሰቦቹ የተትረፈረፈ ምድራዊ ሀብት
ባይኖራቸውም ትዳራቸው በፍቅርና በፈሪሃ እግዚአብሔር ያጌጠ ነበር፡፡ ገና ለጋ ሕፃን ሳለ የዘወትር ምኞቱ መንኩሶ መኖር ነበር፡፡ ውሎ ሲያድር በልቡና
ያሰበውን እውን ያደርግ ዘንድ መንፈሰ እግዚአብሔር አነሣሣው፡፡ መላ ዘመኑን በሥርዓተ አበው በተጋድሎ ሊፈጽም ራቅ ወዳለ
በረሃማ ገዳም ሄደ፡፡ ይህችውም ገዳመ አስቄጥስ ናት፡፡


