Thursday, December 20, 2012

የብሕትውና(የምንኩስና) ኑሮ - ክፍል 3

ምንኵስና በኢትዮጵያ
ከ4ኛው መ/ክ/ዘ በፊት
ሥርዓተ ምንኵስና ወደ ሀገራችን የገባው በኢትዮጵያ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ በአባ ጳኩሚስ ዘመን ቢሆንም የብሕትውና ኑሮ ግን በሀገራችን ከዚያም ቀድሞ እንደነበረ የሚጠቁሙ አንዳንድ መረጃዎች አሉ፡፡
አባ አሞንዮስ፡- ሥርዓተ ምንኵስና ወደ ኢትዮጵያ ከመግባቱ በፊት አሞንዮስ የተባሉ ባሕታዊ በተንቤን ቆላ ደብረ አንሣ በተባለው በረሃ በጾም በጸሎት ተወስነው ይኖሩ ነበር፡፡

Thursday, December 13, 2012

የብሕትውና(የምንኩስና) ኑሮ - ክፍል 2

2. የሥርዓተ ምንኩስና ታሪክ

 2.1   - አባ ጳውሊ  እና  አባ እንጦንስ
    2.1.1-  አባ ጳውሊ
አባ ጳውሊ  እና  አባ እንጦንስ
በተባሕትዎ መኖር ከጥንት ዘመን የመጣ ይሁን እንጂ የብሕትውናን ኑሮ ሥርዓት በወጣለት መልኩ የጀመረው አባ ጳውሊ የተባለው ግብፃዊ አባት ነው፡፡ በንጉሥ ዳክዮስ ዘመነ መንግሥት በክርስቲያኖች ላይ በተነሣው ስደት ምክንያት አባ ጳውሊና ቆይቶም ደግሞ ሌሎች የአካባቢው ክርስቲያኖች በግብፅ በረሃዎች ውስጥ በምናኔ ይኖሩ ነበር፡፡
ይህንን አባ ጳውሊ የጀመረውን ሥርዓት አጠናክሮ ለማስፋፋት ያበቃው ደግሞ አባታችን አባ እንጦንስ ነው (251-356 ዓ.ም.)፡፡

  2.1.2- አባ እንጦንስ
አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ ቆማ በተባለች መንደር ከሀብታም ቤተሰቦች በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወዳጆቹ ገና የ2ዐ ዓመት ወጣት እያለ ስላረፉ በማቴ.19÷21 ላይ ያለውን ትምህርት መሠረት አድርጐ የወረሰውን ሀብት በሙሉ በመሸጥ ለድኾች አከፋፈለና ወደ ግብፅ በረሃ በመውረድ ለ85 ዓመት በተጋድሎ ኖሯል፡፡

Thursday, December 6, 2012

የብሕትውና(የምንኩስና) ኑሮ - ክፍል 1

1.አጀማመር
1.1 በሕገ ልቡና
የብሕትውና ኑሮ የተጀመረው ከሰው ልጅ ወደዚህች ምድር መምጣት አንሥቶ ነው፡፡ ደቂቀ ሴት ከቃየል ልጆች ኑሮና ግብር ተለይተው በደብር ቅዱስ በንጽሕና በቅድስና ይኖሩ እንደነበር ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል( ዘፍ.6÷1-3፤ ሄኖክ 2÷1-2)
አባታችን ሄኖክም በዘመኑ ከነበሩት ግብረ ሰዶማውያን ርቆ፣ ሰዎችን ለጥፋት ውኃ ከዳረገው ኃጢአት ተለይቶ፣ ንጹሕ እግዚአብሔር ንጽሕናን ይሻል በማለት በሕገ ልቡና ተመርቶ በእግረ ገነት ለሰባት ዓመታት በብሕትውና ከኖረ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ፈቃድ ከአካለ ሥጋ ወደ ብሔረ ሕያዋን መነጠቁን መጽሐፈ ሄኖክ ያስረዳል፡፡ የመልከ ጼዴቅም የኑሮ ሥርዓት ይህንኑ የባሕታውያን ሕይወት የተከተለ ነበር( ዘፍ.14÷17-24)፡፡