አባ አርሳንዮስ በ360 ዓ.ም በሮም ተወለደ፡፡ በዘመኑ ትምህርት በሚገባ
የተማረና ለሴናተርነትም መዓርግ የደረሰ ሰው ነበር፡፡ የሮሙ ንጉሥ ቴዎዶስየስ ለልዕልት አርቃድዮስ እና ለልዕልት አኖሬዎስ መምህር
አድርጎ መድቦት ነበር፡፡ በ394 ዓ.ም የሮምን ቤተ መንግሥት ንቆ ትቶ በድብቅ ወደ እስክንድርያ መጣ፡፡ በመቀጠልም ወደ ገዳመ
አስቄጥስ ገብቶ የአባ ዮሐንስ ሐፂር ደቀ መዝሙር ሆነ፡፡ በገዳመ አስቄጥስ አጠገብ በሚገኘው በጴጥራ በምናኔ ይኖር ጀመር፡፡ የታወቁ
ሦስት ደቀ መዛሙርት ነበሩት፡- እስክንድር፣ ዞይለስ እና ዳንኤል፡፡ ድሎት የለሽ ኑሮን በመኖር እና በአርምሞው የታወቀ አባት ነው፡፡
በ434 ዓ.ም ገዳመ አስቄጥስ ለሁለተኛ ጊዜ ከጠፋ በኋላ ወደ ትሮኤ ተራራ ወጣ፡፡ እዚያም በ449 ዓ.ም ዐረፈ፡፡
አባ አርሳንዮስ በቤተ መንግሥት በነበረበት ሰዓት ‹ጌታ ሆይ በድኅነት
ጐዳና ምራኝ› እያለ ይጸልይ ነበር፡፡ እናም ‹አርሳንዮስ ›ሆይ ከሰዎች ተለይ ያን ጊዜ ድኅነትን ታገኛለህ› የሚል ድምጽ ሰማ፡፡
ወዲያውም ቤተ መንግሥቱን ትቶ ወደ ገዳም ገባ፡፡
