ከቅዱሳን ሰማዕታት አንዱ የሆነው ማር ሚና በ 4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተጋድሎውን የፈፀመ ግብፃዊ ሰማዕት ሲሆን ህዳር 15 ቀን የሚነበበው ስንክሳር ቅዱስ ሚናስ በሚል ስያሜ ይገልፀዋል። በሶሪያ ቋንቋ ማር የሚለው ቃል ‘ቅዱስ’ የሚልትርጉም ሲኖረው ለወንድ የሚሰጥ ቅጥያ ሲሆን ለሴት ደግሞ ማርታ ይሆናል ይሄውም ቅድስት ማለት ነው።
ቅዱስ ሚናስ ከእናቱ ከአውፌምያ እና ከአባቱ ከአውዶስዮስ ልዩ ስሙ ኒቆስ ሻቲ በተባለ መንደር በ 276 ዓ∙ም ተወለደ። እናቱ አውፌምያ ልጅ መውለድ ባለመቻሏ ታዝንና ትጨነቅ ነበር። ወደ ቤተ-ክርስቲያን ስትሄድም እናቶች ልጆቻቸውን ሲያቆርቡ ስታይ በማልቀስ ፈጣሪዋን ልጅ እንዲሰጣት ትለምን ነበር። እግዚአብሔርም የልመናዋን ቃል ሰምቶ ወንድ ልጅ ሰጣት።


