Tuesday, October 30, 2012

መልከ ፄዴቅ የክርስቶስ ምሳሌ ክፍል 1


ዕብራውያን 7: 1-10 “ የሳሌም ንጉሥና የልዑል እግዚአብሔር ካህን የሆነ ይህ መልከ ጼዴቅ አብርሃም ነገሥታትን ገድሎ ሲመለስ ከእርሱ ጋር ተገናኝቶ ባረከው፤ ለእርሱም ደግሞ አብርሃም ከሁሉ አስራትን አካፈለው። የስሙም ትርጓሜ በመጀመሪያ የጽድቅ ንጉሥ ነው፥ ኋላም ደግሞ የሳሌም ንጉሥ ማለት የሰላም ንጉሥ ነው። አባትና እናት የትውልድም ቍጥር የሉትም፥ ለዘመኑም ጥንት ለህይወቱም ፍጻሜ የለውም፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ ለዘላለም ካህን ሆኖ ይኖራል።…….”

          አብርሃምና መልከጼዴቅ እንደተገናኙ
ቅዱስ ጳውሎስ ለምን ጠቀሰው
በታላቁ መምህር በገማልያል እግር ሥር በትሕትና የተማረው ምሁረ ኦሪት ቅዱስ ጳውሎስ ከደማስቆ ከተማ ተጠርቶ፣ ሕገ ወንጌልን ተቀብሎ፣ በሕገ ወንጌል ጸንቶ ለወገኖቹ ለዕብራውያን ባስተላለፈው መልእክቱ ስለዚህ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፣ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ (ዕብ.3÷1)፡፡

‹‹ወብነ ሊቀ ካህናት ዐቢይ ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር፤ ዘተለዓለ እምሰማያት›› ማለትም ‹‹እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ስላለን፣ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ፡፡ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፣ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም (ዕብ.4÷14) ብሏቸዋል፡፡
                                        
ሐዋርያው ይኽንን ያለምክንያት አልጻፈላቸውም፡፡ ዕብራውያን ‹‹መከራ ብንቀበል ማን አብነት ይሆነናል?›› እንዳይሉ እና ወደ ኋላ እንዳያፈገፍጉ መከራ የተቀበለውን ኢየሱስ ክርስቶስን አብነት አድርገው፣ መከራውን እየታገሡ በክርስትና ጎዳና እንዲጓዙ ነው፡፡ ዳግመኛም ‹‹ከይሁዲነት ወደ ክርስትና ብንመለስ ማን ያስታርቀናል›› እንዳይሉ ደግሞ ቢመለሱ፣ በሕገ ወንጌል አምነው ቢጠመቁ፣ ሥጋውንና ደሙን ቢቀበሉ፣ ክርስቶስ እርቅን በሞቱ አንድ ጊዜ በመስቀል ላይ የፈጸመ መሆኑን በሚገባ እንዲያውቁ ነው፡፡


- - - ዕብ.3:1 “ስለዚህ፥ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፥ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱቅዱስ ጳውሎስ በዚህ በእብራውያን መልእክቱ ያተኮረው ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሁሉ የሚበልጥ መሆኑን ማስረዳት ነው፡፡ ይህንንም የሚያስረዳው ደግሞ በንፅፅር ነው፡፡ ከነቢያት ስለመብለጡ የእነሱን ንግግርና የእሱን ንግግር በማነፃፀር አስረዳ፡፡ ከዚያም በኅላ ደግሞ ከመላእክት መብለጡን አስረድቷል፡፡ አሁን ደግሞ ከካህናት መብለጡን ለማስረዳት ያመጣል፡፡ ከካህናት መብለጡንም ሲያስረዳ ዋናወቹ ምክንያቶች 1) በክህነቱ 
             2) በመስዋእቱ 
            3) መስዋእቱ በቀረበበት ድንኳን መሆኑን ያስረዳል፡፡ 
ስለክህነቱም ዕብ.51-10 በዕብ. 620 71-28 81-3 ባሉት አስረድቷል፡፡

           የጌታችን ክህነትና የመልከ ፄዴቅ ክህነት
ክህነት ምንድን ነው? 
- - - አገልግሎት ሲሆን መሾምን መመረጥን ያመለክታል፡፡ በመፅሃፍ ቅዱስም ከአዳም ጀምሮ የተለያዩ ሰወች ለዚህ ክህነት በሰውም በእግዚአብሄርም ሲመረጡ ያሳየናል፡፡ 


የሊቀ ካህናቱ ሥራ ምን ነበር?
በኦሪቱ የሊቀ ካህናት ሥራ ቤተ መቅደስን ማስተዳደር እና ካህናትን መቆጣጠር፣ በሸንጐም ላይ ሊቀ መንበር መሆን ነበር (1ኛሳሙ 3÷12፣ 2ኛነገ 12÷7፤ 22÷4፤ ማቴ.26÷57-65)፡፡ ከዚህም ሌላ ሊቀ ካህናቱ በማስተሥረያ ቀን ስለ ራሱና ስለ ሕዝቡ ልዩ መሥዋዕት ያቀርባል፡፡ በዚህም ቀን በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ገብቶ በታቦቱ ላይ ደም ይረጫል (ዘሌ 16÷34)፡፡

የእሥራኤል ሕዝብ በሰባተኛው ወር፣ በአሥረኛው ቀን (ጥቅምት 1ዐ ቀን ገደማ) ኃጢአታቸውን ይናዘዙ ነበር፡፡ ሊቀ ካህናቱም የማዕረግ ልብሱን አውልቆ (በትሕትና) ሌላ ልብስ በመልበስ መጀመሪያ ለራሱ እና ለካህናቱ ቀጥሎም ለሕዝቡ መሥዋዕት ያቀርባል፡፡ የታቦቱም መክደኛ የሥርየት መክደኛ የሚባለው ስለ ሥርየተ ኃጢአት የሚፈሰው ደም ስለሚረጭበት ነው፡፡

መልከ ፄዴቅ ማነው? 
- - ዕብ.7:3 “አባትና እናት የትውልድም ቍጥር የሉትም፥ ለዘመኑም ጥንት ለህይወቱም ፍጻሜ የለውም፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ ለዘላለም ካህን ሆኖ ይኖራል።” 
መልከ ጼዴቅ የሳሌም ንጉሥ ነበር፡፡ ይህም የሰላም ንጉሥ ማለት ነው፡፡ ሳሌም በሄኖን አቅራቢያ የነበረ የመልከ ጼዴቅ ከተማ ነው (ዘፍ.14÷18፤ ዮሐ.3÷23)፡፡ መልከ ጼዴቅ የሰላም ንጉሥ የተባለበት ምክንያት የአገሩ ሰዎች ሄደው ንገሥልን ቢሉት በጎልጎታ የተቀበረውን የአዳም አፅም ይጠብቅ ስለነበር ያስጠበቀኝን ትቼ አይሆንም ብሏቸዋል፡፡ ይሁን እንጂ ተጣልተው ወደ እርሱ ሲመጡ የማታ ማታ ያስታርቃቸው፣ ሲከራከሩም እውነት ይፈርድላቸው ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ ንጉሠ ሰላም ወጽድቅ ተብሏል፡፡

ለመልከ ጼዴቅ አባቱ እገሌ ነው እናቱ ደግሞ እገሊት ናት ተብሎ አልተነገረለትም፡፡”ወአልቦ ጥንት ለመዋዕሊሁ ወኢማኀለቅ ለሕይወቱ” በዚህ ቀን ተወለደ በዚህ ቀን ደግሞ ሞተ ብሎ የተናገረለት መጽሐፍ የለም፡፡ ምነው በስንክሳር ተጽፎ የለምን? ቢሉ በሌዋውያን መጽሐፍ ስላልተጻፈ ነው፡፡ “በአምሳሊሁ ለወልደ እግዚአብሔር ይነብር ክህነቱ ለዝሉፉ “ - የመልከ ጼዴቅ ክህነት ለወልደ እግዚአብሔር ክህነት በምሳሌነቱ ለዘለዓለሙ ጸንቶ የሚኖር›› ነው፡፡

አበ ብዙኃን አብርሃም ኮሎዶጎሞርንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ነገሥታት ወግቶ ድል አድርጎ በተመለሰ ጊዜ ምሳሌውን እንዲያይ ተፈቅዶለት ነበርና ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ መልከ ጼዴቅ ሄደ፡፡ መልከ ጼዴቅም በመንፈስ ተረድቶ በሌዊ ሸለቆ ሊቀበለው ወጣ፡፡
             ይህ ሲባል መልከ ፄዴቅ ሰው አይደለም ማለት አይደለም ዘሩ ከካም ዘር ነበረና በሙሴ መፃህፍት አልተገለፀም ለማለት ነው፡፡ ይህ የተመረጠ ሰው አፅመ አዳምን እንዲጠብቅ የታዘዘ በብህትውና የሚኖር ነው፡፡ የመልከ ፄዴቅ ክህነትም ሙሴ አሮንን በሾመበት ሥርአት ቅብዕ አፍልቶ መስዋእተ እንስሳ ሰውቶ ፡ልዩ ልዩ ህብር ያላቸውን አልባሳት አልብሶ የሾመው ሰው የለም፡፡ይልቁንም እግዚአብሄር መረጠው በማይታወቅ ግብርም ሾመው እንጂ፡፡ አሮንና ልጆቹ በሙሴ እጅ ሙሴም በመልአኩ እጅ እንደተሾሙ (ሐዋ 66) መልከፄዴቅ ግን ሹመቱ ከእግዚአብሄር ነውና ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስዳሩ ግን በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ ለዘላለም ካህን ሆኖ ይኖራል።ያለው ለዚህ ነው፡፡ለዘላለምማለቱም እስከ ህይወቱ ፍፃሜ ማለቱ ነው፡፡በዚህም ምክንያት ክህነቱ ከሌዋውያን ክህነት ፍፁም የተለየ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ እንደሌዋውያን ክህነትም የእንስሳት መስዋእት አይሰዋም መስዋእቱ ንፁህ ስንዴና ወይን ነውንጂ፡፡ በዚህም ተነስቶ ቅዱስ ጳውሎስ - - ዕብ.7:11 እንግዲህ ህዝቡ በሌዊ ክህነት የተመሠረተን ሕግ ተቀብለዋልና በዚያ ክህነት ፍጹምነት የተገኘ ቢሆን፥ እንደ አሮን ሹመት የማይቈጠር፥ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ግን የሆነ ሌላ ካህን ሊነሳ ወደፊት ስለ ምን ያስፈልጋል? ብሎ ይጠቅሰዋል፡፡
ነገረ መልከ ፄዴቅ በእብራውያን

1.           የሌዋውያን ካህናትን በክህነት ይቀድማቸዋል እርሱ ከአብርሃም በፊት ነበረና --- ዘፍ 1418-21 
2.           ክህነቱ ዘላለማዊ ነው - ዕብ 73 ለብዙ ዘመናት በብህትውና እንደኖረና ክህነቱም ለልጅ ልጅ የሚተላለፍ ስላልሆነ ይህ ተጠቅሷል፡፡ የሌዋውያን ክህነት ግን ሞት በየጊዜው አለባቸውና ዕብ.7:23 “እነርሱም እንዳይኖሩ ሞት ስለ ከለከላቸው ካህናት የሆኑት ብዙ ናቸውእንዲል፡፡ 
3.           ሌዋውያንን አስራት አስወጥቷል - - - ሌዋውያን ከህዝቡ አስራትን እንዲቀበሉ ስርአት አላቸው፡፡ ነገር ግን መልከ ፄዴቅ ከአብርሃም አስራትን በተቀበለ ጊዜ ከእነርሱ ክህነት የእርሱ ክህነት እንዲበልጥ ታወቀ፡፡ 
4.   ሌዋውያንን ባርኳል - - - እጃቸውን ዘርግተው ህዝቡን የሚባርኩት የሌዋውያን ካህናት በአብርሃም በኩል በመልከ ፄዴቅ ተባርከዋል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ዕብ.7:6-7” ትውልዱ ከእነርሱ የማይቈጠረው ግን ከአብርሃም አሥራትን አውጥቶአል፥ የተስፋ ቃል የነበረውንም ባርኮአል።ትንሹም በታላቁ እንዲባረክ ክርክር የሌለበት ነገር ነው።እንዲል፡፡ 
5.   መስዋእቱ የሚሞቱ እንስሳት አይደሉም - - - የሌዋውያን ካህናት መስዋእታቸው ከእንስሳት የሚዘጋጅ ሲሆን የመልከፄዴቅ መስዋእት ግን ከንፁህ ስንዴና ወይን የሚዘጋጅ ነው ፡፡ ይህም የክርስቶስ ስጋውና ደሙን የሚያመለክትልን ነው፡፡ 

         ቅዱስ ጳውሎስ ሁሉንም በዚህ ምእራፍ አጠቃልሎ እንዳስቀመጠው ክህነተ መልከፄዴቅ ክህነተ ሌዋውያንን ይበልጣል፡፡ የጌታችን የመድሃኒታችን የኢየሱስ ክህነት ደግሞ ከመልከ ፄዴቅ ክህነት ይበልጣል፡፡ መልከፄዴቅ ለጌታችን አምሳል ነበርና፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ጳውሎስ ንግግር አባታችሁ አብርሃም አብርሃማዊ ካልሆነው ከመልከ ፄዴቅ የሚያንስ ከሆነ ይልቁንም ከመልከ ፄዴቅ አምላክ ከክርስቶስማ እንዴት አያንስም? የመልከ ፄዴቅ ክህነት ከእናንተ ከተሻለ ይልቁን የጌታማ እንዴታ
          መስዋእታችሁ ከመልከ ፄዴቅ ካነሰ ይልቁን እንዴት ከጌታ ትበልጣላችሁ ለመልከ ፄዴቅ አስራት ካወጣችሁ ለጌታማ እንዴት አብዝታችሁ ማድረግ አይገባችሁ? በመልከ ፄዴቅ ከተባረካችሁ ይልቁንም መስጠትና መንሳት ለእርሱ ብቻ ከሚቻለው ከወልደ እግዚአብሔርማ እንዴት አብልጣችሁ መጠቀም ይገባችኋል ለማለት ተናገረው፡፡አላማውም የጌታን ታላቅነትና የባህርይ አምላክነት በመመስከር ልቆ ከሚልቁት እነርሱንም ያላቃቸው እርሱ መሆኑንና ይህ ስልጣን እንዳለው ለማስታወቅ ነበር፡፡
የጌታችን ክህነት በምን የተለየ ሆነ?

1.           የባህርይው ስለሆነ - - - ክርስቶስ ሁሉንም ነገር ያደረገው በስልጣኑ ነው፤ ሙትን ያስነሳው ድውያኑን የፈወሰው ያስተማረው የሞተው የተነሳው ያረገው - - - በስልጣኑ ነው፡፡ የጌታችን የክህነት አግልግሎት ዋናው ራሱን በመስቀል ላይ መስዋእት አድርጎ ማቅረቡ ነው፡፡ ይሄውም ስጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ነፍሱን ክሶ አለሙን የመቀደስና የማንፃት ሞትንና የሞትን አበጋዝ ዲያቢሎስን በሞቱ ድል መንሳቱ ነው፡፡ ይህ ነው የጌታችን ከእርሱ ለእኛ የተደረገልን የክህነት አገልግሎት፡፡ ሞቱ ደግሞ በስልጣኑ እንደሆነ ሞቱን በስልጣኑ ፈፀመው መባሉ ደግሞ ክህነቱ የባህርይው መሆኑን ለመግለጥ ነው፡፡ ከማንም አልተቀበለውም ማንምም ከእርሱ አይወስድበትም፡፡ይህም ማለት ባህርይ መለኮቱ ባህርይ ትስብእቱን በተዋህዶ አከበረው እንጂ ሌላ የሚሰጠው እርሱም የተቀበለው የለም፡፡ ስለዚህ እርሱ እንደመልከፄዴቅ በስውር እንደ አሮን በገሃድ የተሾመ አይደለም እርሱ ሰጪ እንጂ ተቀባይ አይደለምና፡፡ዮሐ 13 “ሁሉ በእርሱ ሆነእንዲል፡፡ ዕብ.5:5 “እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ ሊቀ ካህናት ሊሆን ራሱን አላከበረም ነገር ግን። አንተ ልጄ ነህ እኔ ዛሬ ወልጄሃለሁ ያለው እርሱ ነውሲል የቃልን በስጋ መወለድ ሐዋርያው ተናግሯል፡፡ ይህም በእርሱ ፈቃድ ብቻ ሳይሆነ በአባቱም ፈቃድ መሆኑን ለመናገር ነው፡፡ 
2.           ዘላለማዊ ነው - - - “ዘላለምየሚለው ቃል ለፍጡርና ለፈጣሪ ሲቀፅል አንድ እንዳልሆነ አንባቢ ልብ ይሏል፡፡ ስለዚህም የመልከፄዴቅ ክህነት ህይወቱ እስኪያልፍ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ የጌታችን ክህነት ዘላለማዊነቷ እርሱ ሽረትና ሞት የሌለበት አምላክ ስለሆነ ነው፡፡ በስጋ ሞተ የምንለውም ነፍሱ ከስጋው ተለየች ለማለት እንጂ ከተዋህዶ በኅላ መለኮትና ትስብእት የተለያዩበት ቅፅበት የለም፡፡ስለዚህ ለክህነቱ ተቀባይ አያስፈልገውም የባህርይ ክህነትም ከእርሱ በቀር ገንዘብ ሊያደርገው የሚቻለው የለምና፡፡ ዕብ.7:24 “እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለውተብሎ ተፅፏልና፡፡ዕብ.7:24-25 “እርሱ ግን ለዘላለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው፤ስለ እነርሱም ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል።” - - - እነዚህ ጥቅሶች ጌታችንንአማላጅነው በማለት የሚያስተላልፉት መልእክት የለም፡፡ የሰው ልጆች ሁሉ በክርስቶስ ቤዛነት አምነው ሲመጡ የእግዚአብሄር ቤተመቅደስ ሆኑ የሚባሉት በስመ ስላሴ ተጠምቀው የክርስቶስን ስጋና ደም ሲቀበሉ ብቻ ነው፡፡ የክርስቶስ ስጋና ደም ደግሞ እንደ ኦሪት መስዋእት በአንድ ቀን የሚያልቅ በጊዜ ብዛት የሚለውጥ የሚበላሽ አይደለም ፡፡ ነገር ግን ሁልጊዜ አዲስና ለዘላለሙ በህይወት የሚኖር ነው፡፡ሕያውመባሉም ነፍስ ስለተዋሃደው ሳይሆንመለኮትስለማይለየው ነው፡፡ - - - ይህ ሕያው ስጋውና ደሙ ሁልጊዜ ሰውን ወደ እግዚአብሄር ሲያቀርብ የሚኖር ከእግዚአብሄርም ጋር የመታረቂያው ብቸኛ መንገድ በመሆኑ አማለደን (አስታረቀን) ሲል ገልፆታል፡፡ሊያማልድ በህይወት ይኖራልየሚለውንም በጥሬ ንባቡ ከሆነ ጌታችን አሁንም በስጋ ህይወት በምድር አለ ያስብልብናልና፡፡ 
3.           ፍፁም ነው - - - የሌዋውያን ክህነት ፍፁም አይደለም የመልከ ፄዴቅም ዘላለማዊ እንጂ (አንፃራዊ) ፍፁም አልነበረም፡፡ ማንንም ወደ ገነት መመለስ አልተቻላቸውምና፡፡ እነርሱም ራሳቸው በአዳም የመጀመሪያ ሃጢአት ተይዘዋልና፡፡እርሱ ራሱ ደግሞ ድካምን ስለሚለብስዕብ 728 ዕብ 52 ተብሎባቸዋልና፡፡ ለጌታችን ግን ሃጢአት የለበትም ተብሏል፡ 1 ዮሐ35 ከዚህ የተነሳ ክህነታቸው ፍፁም አይደለም፡፡በመሆኑም እለት እለት ወደ ቤተ መቅደስ እየገቡ የሚሞት መሥዋእት ማቅረብ ግድ ሆነባቸው፡፡ ዕብ 96-7 እርሱ ግን ክህነቱ ፍፁም መሥዋእቱም ህያው ስለሆነ እለት እለት መስዋእት ማቅረብ አላስፈለገውም፡፡ ዕብ.7:27 “እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና።እንዳለ አንድ ጊዜ ባቀረበው መስዋእት ለዘላለም አንፅቶን ሊኖር ይቻለዋልና፡፡ ቆላ.1:19-20 “እግዚአብሔር ሙላቱ ሁሉ በእርሱ እንዲኖር፥ በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ሁሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና።እንዲል 

ይቆየን      
ክፍል ይቀጥላል
 ከሉቨን ከተማ - ቤልጅየም

-     ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዋቢ፦ -      መጽሐፍ ቅዱስ
-                                      ወንጌል ትርጓሜ
               የቅዱስ ጳውሎስ መልዕክታት ትርጓሜ
               ሁለቱ ኪዳናት”  በእብራውያን መልእክት ትርጓሜ ላይ የተመሰረተ መጽሐፍ

6 comments:

  1. Egziabher be hiwot yitebikilin! Kale hiwot yasemalin!

    ReplyDelete
  2. የድንግል ማርያም ልጅ በሰላም ጠብቆ ይመልስህ::

    ReplyDelete
  3. The west version of Christianity always confuses those concepts related to Ethiopiawinet. The historical evidences related to Melke Tsedek, who was a True Ethiopian is a typical case. There is no where in the world that has a blue print of Melke Tsedek except Ethiopia. You need to do further research beyond our "Tirguame Mestehaft", which most of the time is molded per the Copts version, to make your presentation complete. I will advise you to look into ethkogserv.org and some of the books by Meri Ras Aman Belay!

    ReplyDelete
  4. Tebarek DN Melaku melkam timihirt new

    ReplyDelete