Monday, August 20, 2012

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ


Click For PDFልደትና ትምህርት 
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 25 ቀን 1928 .. በዘመነ ዮሐንስ በዓድዋ ከተማ በመደራ አባ ገሪማ ገዳም አካባቢ ከካህን ቤተሰብ፣ ከአባታቸው ከአፈ መምህር ገብረ ዮሐንስ ወልደ ሥላሴና ከእናታቸው ከወ/ አራደች ተድላ ሲወለዱ ገብረ መድኅን የተባሉት አቡነ ጳውሎስ፣ በጥንታዊው አባ ገሪማ ገዳምና በአዲስ አበባ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ መንፈሳዊ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡

በወቅቱ ሁለተኛው ፓትርያርክ በነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ አማካይነት ለከፍተኛ ትምህርት ወደ አሜሪካ ተልከው ከሩሲያው የቅዱስ ቭላድሚር ቲኦሎጂካል ሴሚናሪ በኦርየንታልና በምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ባለው የነገረ መለኮት ይትበሐል (ትምህርት) 1954 . ዲፕሎማ አግኝተዋል፡፡ ቀጥሎም በየል ዩኒቨርሲቲ በኦሪየንታል፣ በምሥራቅና በምዕራባውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል ስላለው የነገረ መለኮት ትምህርት አመለካከትና ልዩነት ባችለር ኦፍ ዲቪኒቲ ዲግሪን 1958 . ሲያገኙ፣ ከፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ማስተርስ ኦፍ ቴኦሎጂ ዲግሪን 1964 .. ተቀብለዋል፡፡

በዚያው ዩኒቨርሲቲ 1980 .. የዶክትሬት (ፒኤችዲ) ዲግሪያቸውን ያገኙት ስለእግዚአብሔር ህልውና እና ስለፍልሰታ ማርያም በጻፏቸው የጥናት ድርሳኖች ነው፡፡ በተለይ ‹‹ፍልሰታ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ፍልሰትና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የነገረ ማርያም ትምህርት ትውፊት›› (Filsata: The Feast of the Assumption of the Virgin Mary and the Mariological Tradition of the Ethiopian Orthodox Church) የተሰኘው የመመረቂያ ድርሳናቸው የኢትዮጵያ የእምነት ውሳኔ ከሌሎቹ እህት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያለውን ዝምድና የሚያነፃፅር፣ በማንም ኢትዮጵያዊ ተመራማሪ ያልተሞከሩትን ወይም ሚዛናዊ ትችት ያልቀረበባቸውን በኢትዮጵያ ውስጥ የተነሱ ልዩ ልዩ ጥያቄዎችና ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ፋይዳ ጎልቶ የቀረበበት መሆኑ ይነገርለታል፡፡ 

ይኸው የአቡነ ጳውሎስ የዶክትሬት ዲግሪ መመረቂያ የጥናት ጽሑፍ ታትሞ ከሦስት ሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ገለጻ (ሌክቸር) ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ በመድረኩም በአገሪቱ በጥንታዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የተመሠረተ የዘመናዊ የኦርቶዶክስ ነገረ መለኮት ጥናት መሥራችና የዘመናዊ ኦርቶዶክስ ነገረ ማርያም አባት የሚል መጠርያም ተንፀባርቋል፡፡ 


አገራዊ አገልግሎት

የአቡነ ጳውሎስ ዜና ሕይወት እንደሚዘክረው አባ ገብረ መድኅን በሚባሉበትና የውጭ ትምህርታቸውን አጠናቀው ከአሜሪካ ከተመለሱ በኋላ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሁለገብ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ 

የጎፋ መካነ ሕያዋን ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የጥበበ ዕድ የካህናት ማሠልጠኛ በማቋቋም በመምራት፣ የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዲን፣ የታሪክ፣ የድርሰትና የስብከተ ወንጌል፣ የጋዜጦች፣ የመጽሔቶችና የሬዲዮ መምርያ የበላይ ኃላፊ፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማዕከል በዘመናዊ መልክ በማቋቋም አገልግለዋል፡፡ ሁለተኛው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለንተናዊ ሕይወት በዘመናዊ መልክ ለማደራጀትና ለመለወጥ ሲነሱ ፋና ወጊ ከሆኑት አንዱ አባ ገብረ መድኅን (አቡነ ጳውሎስ) ናቸው፡፡ 

ቃለ አዋዲ የተሰኘውን የመመርያ ደንብ በማውጣት ምእመናን በሰበካ ጉባዔ፣ ካህናትን በካህናት ማሠልጠኛ ትምህርት ቤቶች በሚያደራጁበት ወቅት ግንባር ቀደም በመሆን ተሳትፈዋል፡፡ እንዲሁም የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ዋና ዳይሬክተርና የስደተኞች አገልግሎት ዋና ጸሐፊ፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የበላይ ኃላፊ በመሆን ሲሠሩ፣ ከአገር ውጭም 1950 .. ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱን በመወከል በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር ቀዋሚ ኮሚቴ አባል ነበሩ፡፡ 1960 .. ካናዳ ላይ ተደርጎ በነበረው ዓለም አቀፍ ኤክስፖ ኢትዮጵያ ስትሳተፍ የታሪክና የእምነት ክፍል ኃላፊ በመሆን ለስምንት ወራት በሰጡት አኩሪ አገልግሎት በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ‹‹ፋዘር ኤክስፖ›› የሚል ስያሜ አግኝተው ነበር፡፡


ፓትርያርኩ አቡነ ቴዎፍሎስ የአባ ገብረ መድኅንን የሥራ ውጤትና ታማኝነት በማየት ለጳጳስነት ከማጨታቸው በፊት መስከረም 18 ቀን 1967 .. የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አድርገዋቸው ነበር፡፡

ከጵጵስና እስከ ፕትርክና

1967 .. የመንግሥት ለውጥ በሚደረግበት ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ከፈታኝ ሁኔታ ለማውጣት የበቃ አመራር ለመስጠት እንዲያስችል እንቅስቃሴ ያደረጉት የወቅቱ ፓትርያርክ፣ አባ ገብረ መድኅን ገብረ ዮሐንስን ለውጭ አገር አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነትና ለማኅበራዊ አገልግሎት ጵጵስና አድርጎ ቅዱስ ሲኖዶሱ እንዲመርጣቸው በማድረጋቸው፣ መስከረም 16 ቀን 1968 .. ብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ተብለው ተሹመዋል፡፡
ይሁን እንጂ ደርግ እርሳቸውንና አብረዋቸው የተሾሙትን አቡነ ባስልዮስና አቡነ ጴጥሮስን ጨምሮ ለእስር ዳረጋቸው፡፡ ሰባት ዓመትም አሰራቸው፡፡ 1974 .. ከእስር ቢለቀቁም ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ከቤተ ክህነት በጡረታ እንዲገለሉ በመደረጋቸው ባሕር ማዶ ሔደው በእስር ምክንያት ያቋረጡትን የዶክትሬት ትምህርታቸውን ለመቀጠልና ለማጠናቀቅ ዕድል ፈጠረላቸው፡፡ በአሜሪካ የተለያዩ ግዛቶችም ለኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች ምዕመናን አገልግሎት የሚሰጡ ሰባት አብያተ ክርስቲያናትን አቋቁመዋል፡፡ የደርግ መንግሥት 1983 .. መውደቁን ተከትሎ ከስደት የተመለሱት አቡነ ጳውሎስ በዓመቱ በተደረገው ምርጫ አምስተኛው ፓትርያርክ ሆነው በመመረጥ ሕይወታቸው እስካለፈበት እስከ ነሐሴ 10 ቀን 2004 .. ድረስ 20 ዓመት 36 ቀን የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን መርተዋታል፡፡ ለረዥም ዓመታት ያገለገሉ የመጀመሪያው አባትም ሆነዋል፡፡

በፓትርያርክነታቸው ቀዳሚ ዘመን ካከናወኗቸው ተግባራት በዓቢይነት የሚጠቀሱት በወታደራዊው መንግሥት የተወረሱ የቤተ ክርስቲያኒቷን ሀብቶች ማስመለሳቸው፣ ተዘግቶ የነበረውና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ክልል ውስጥ የተካተተው ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን ዳግም ማስከፈታቸው፣ የጤና ሳይንስን ጨምሮ ልዩ ልዩ ኮሌጆችም በየአካባቢው እንዲቋቋሙ አብያተ ክርስቲያናት በልማትና ማኅበራዊ ሥራ ውስጥ ተሳታፊ ሆነው አቅማቸው እንዲጎለብት ማድረጋቸው ነው፡፡ 

በተለይ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን የመንበረ ፓትርያርክ ሕንፃ ማስገንባታቸው፣ ያለፉት የቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን አባቶች የተገለገሉባቸውን ንዋያተ ቅድሳትና ጥንታውያን የብራና መጻሕፍትንና ታሪካዊ ቅርስ ቅርሶችን አካቶ የያዘ ዘመናዊ ሙዚየም ማስገንባታቸው ልዩ ሥፍራ አግኝቷል፡፡ ለዘመናት በደሳሳ ቢሮ ይኖር የነበረው ጠቅላይ ቤተክህነት ሁለገብ አገልግሎት የሚሰጡ የተለያዩ ፎቆች ባለቤትም ሆኗል፡፡ ሌላው ስኬታቸው በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን በእንግሊዝ ተዘርፈው ከተወሰዱ ቅርሶች መካከል ታቦትና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት እንዲመለሱ ማስደረጋቸው ነው፡፡ 

በቅዱሳት መጻሕፍት ሕትመትም፣ በዘመናቸው በርካታ የአንድምታ ትርጓሜ መጻሕፍት ታትመዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ የሚገልጽ በቅዱስ ሲኖዶስና ሊቃውንት ጉባዔ ተዘጅቶ በአማርኛና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች ታትሞ የተሰራጨው ለመጀመርያ ጊዜ በእርሳቸው ዘመን ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና መሠረት የግእዙን መጽሐፍ ቅዱስ መሠረት ያደረገ መጽሐፍ ቅዱስ በሊቃውንቱ አማካይነት ተዘጋጅቶ 2000 .. ታትሞ እንዲወጣ ማድረጋቸው፣ በተከታታይ ታትሞ ቢሰራጭም አንዳንድ ግድፈት ስለተገኘበት እንደገና ከበፊቱ በበለጠ በጥራት ታርሞና እንከን የለሽ ሆኖ ለሦስተኛ ጊዜ እንዲታተም በሰጡት መመርያ መሠረት፣ ኮሚቴው ብዙ ጊዜ ወስዶ በጥንቃቄ ካረመ በኋላ በአሁን ወቅት ለሕትመት ዝግጁ መሆኑ ይነገራል፡፡ አቡነ ጳውሎስ ለመጀመሪያ ጊዜ የግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ አማርኛው በአንድ ጥራዝ ተጠቃልሎ እንዲዘጋጅ በሰጡት መመሪያ መሠረት ተጠናቅቆ ለኅትመት መቅረቡ ከትሩፋታዎቻቸው መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ 

ዓለም አቀፋዊ ሰውነት 

በኢትዮጵያ 1967 .. በተደረገው የመንግሥት ለውጥ ሳቢያ በቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ በተፈጠረው ሁኔታ ከኦርዬንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ጋር የነበራት ግንኙነት ቀዝቅዞ በወቅቱም ለነበሩት መሪዎችም ዕውቅናም አልተሰጠም ነበር፡፡ 

ኢትዮጵያ በራሷ ፓትሪያርክ መመራት ከጀመረችበት 1951 እስከ 1968 . ድረስ የነበረው የኢትዮጵያና የግብፅ (እስክንድሪያ) አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት የተቋረጠው ደርግ ፓትርያርኩን አቡነ ቴዎፎሎስን አውርዶና አስሮ ሌላ ፓትርያርክ እንዲሾም ባደረገበት ጊዜ ነው፡፡ በወቅቱ ፓትርያርኩ አቡነ ሺኖዳና ጥንታዊቷ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ለውጡን መቃወም ብቻ ሳይሆን ሕጋዊ እውቅና ባለመስጠት ለዓመታት ቆይተው ነበር፡፡ቀኖናውን የጣሰ ተግባርና ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ተፈጽሟል፡፡ የአቡነ ቴዎፍሎስ ሞት ካልተረጋገጠ በስተቀር ሌላ ፓትርያርክ አናውቅምብለዋል፡፡ የሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት በምልዐት የታደሰው የአቡነ ቴዎፍሎስ ዜና ዕረፍታቸው ታውቆ አጽማቸው ሐምሌ 4 ቀን 1984 .. በክብር ካረፈ በኋላ ሐምሌ 5 ቀን 1984 . የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በዓለ ሲመት ከተፈጸመ በኋላ ነው፡፡

በተለይም ሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት በመሪዎች ደረጃ ይፋዊ ግንኙነት በአዲስ አበባ የተፈጸመውም አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ በአቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ 15 በዓለ ሲመት ላይ ሐምሌ 5 ቀን 1999 .. በተገኙበት ጊዜ ነበር፡፡ በአቡነ ቴዎፍሎስ ዘመን የተጀመረውን ግንኙነታቸውንም በአቡነ ጳውሎስ ዘመንም ቀጥለውበታል፡፡ አቡነ ሺኖዳ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሁለት ሺሕ ዓመት ኢዮቤልዩ የሆነውን እሥራ ምእትን (የሦሰተኛውን ሺሕ/ሚሊኒየም ዋዜማ) ባከበረችበት የመስቀል ደመራ በዓል በመስቀል አደባባይ በመገኘት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡ 

ቅዱስ ፓትርያርኩ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋራ በተደጋጋሚ ባደረጉት ሐዋርያዊ ጉዞ ከኦሬንታል፣ ከምሥራቅና ምዕራብ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ግንኙነቱ በመጠናከሩ የፓትርያርኩም ልዕልና በሥራ በመታጀቡ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት እስከ መሆንና እስከ ሕልፈተ ሕይወታቸው ድረስ በመሪነት እንዲዘልቁ አድርጓቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት መሥራች አባል በሆነች 58 ዓመት ለዚህ ከፍተኛ ደረጃ የበቃችበትም ዐቢይ ክንውን ነው፡፡
 
በኅብረቱ ውሰጥ ያለነው የክርስቲያኑን ዓለምና የተወሰነ የኅብረተሰብ ክፍል ብቻ ለማገልገል ሳይሆን መላውን ዓለም ለማገልገል ጭምር ነውበማለት በየካቲት 1998 .. በብራዚል ፖርቶ አሌግሬ ከተማ በፕሬዚዳንትነት በተመረጡበት ጊዜ የተናገሩት አቡነ ጳውሎስ፣ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ቀንድ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃም ሰላም ይሰፍን ዘንድ ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ ለሰላምና ሰብአዊ አገልግሎት ጥረታቸውም ከተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ኮሚሽን ይበልታን አግኝቶ የናንሰን ሜዳይን እንዲሸለሙ አድርጓቸዋል፡፡ 
በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት በሁለቱ አገሮች መካከል ሰላም ለማስፈን ያደረጉት ጥረት፣ የኤችአይቪ ኤድስ ስርጭት ለመግታትና ሕሙማን ለመርዳት ያበረከቱት አስተዋጽኦ፣ እንደዚሁም በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የሚገኙ የቤተ ክርስቲያንዋ አካላትን በማጠናከርና በማስፋፋት ያስመዘገቡት ተጨባጭ ውጤት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ሆነው እንዲመረጡ አስችሏቸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ ቤተ ክርስቲያኒቷን ከመሩ አባቶች መካከል ከፍተኛ ዕውቀት የነበራቸውና አነጋጋሪ የነበሩት ፓትርያርኩ፣ ወደ ሥልጣን ከመጡ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያኒቱን በማጠናከር በዓለም አቀፍ ደረጃም ግንኙነቷና ተሰሚነቷን በማሳደግ የላቀ አስተዋጽኦ እንደነበራቸው በብዙዎች ዘንድ ይነገርላቸዋል፡፡ 

የመጨረሻው መጨረሻ

ከብፁዓን ወቅዱሳን አቡነ ባስልዮስና አቡነ ቴዎፍሎስ፣ አቡነ ተክለሃይማኖትና አቡነ መርቆሬዎስ በኋላ አምስተኛው ፓትርያርከ ሆነው የመጡት አቡነ ጳውሎስ ለሁለት አሠርት ፕትርክናውን መርተዋል፡፡ በዘመነ ዮሐንስ ነሐሴ 10 ቀን 2004 .. ከማረፋቸው 36 ቀናት በፊት በዓለ ሲመታቸው በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሲከበር ካስተላለፉት መልእክት ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል፡፡ 

ባለፉት 53 ዓመታት ፕትርክና ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ድሎችን ተጎናጽፋለች፡፡ መላ ኢትዮጵያ እንደ አንድ የኮፕቲክ ሀገረ ስብከት ትቆጠር የነበረችበት ታሪክ አክትሞ ቤተ ክርስቲያናችን በአሁኑ ጊዜ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ወደ 70 ያህል አህጉረ ስብከት ያሏት ናት፤ ከኢየሩሳሌም በስተቀር በውጭ ሀገር ምንም ዓይነት ሀገረ ስብከት ያልነበራት ቤተ ክርስቲያናችን በአሁኑ ጊዜ በአፍሪካ፣ በአውሮፓ፣ በመካከለኛው ምሥራቅ፣ በሰሜን አሜሪካ፣ በደቡብ አሜሪካ፣ በካናዳ፣ በአውስትራሊያ በአጠቃላይ በዓለም ዙሪያ ሁሉ ተስፋፍታለች፤ በሌላ አገላለጽ ከሀገራዊነት ወደ ዓለም አቀፋዊነት ተሸጋግራለች፡፡ ለቀደምት አበው ምስጋና ይድረሳቸውና፣ የቀደሙት አባቶቻችን ከፍተኛው የክህነት ሥልጣን ይገባታል ብለው አጥብቀው የታገሉት ቤተ ክርስቲያናችን አሁን የተቀዳጀችውን ዓለም አቀፋዊ ልዕልናና የመስፋፋት ዕድል ለማጎናጸፍ ነው፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይድረሰውና ተሳክቶአል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በዓለም ዙሪያ የሆነው ሐዋርያዊ ግዳጅዋን ሙሉ በሙሉ ተወጥታለች ባንልም ለተሻለ ሐዋርያዊ ሥራ የሚያገለግሉ የጠነከሩ መሠረቶችን በዓለም ዙሪያ ሁሉ መሥርታለች፤ አሁን እነርሱን የማጎልበት ሥራን መሥራት አለብን፡፡ በዛሬው ዕለት የምናከብረው የቤተ ክርስቲያናችን በዓል ያን ሁሉ የአባቶቻችንን ጥረትና ተጋድሎ በማስታወስ የቀረንን ሐዋርያዊ ሥራ ዳር ድንበር ለማድረስ ቃላችንን የምናድስበት በዓል ነው፤ ለዚህም ነው በዓሉ የቤተ ክርስቲያን በዓል ነው የምንለው፡፡
 

‹‹የቤተ ክርስቲያን ሥራ በየጊዜው እየሰፋና እያደገ የሚሄድ ቀጣይ ሥራ እንጂ በአንድ ዘመን፣ በአንድ ቦታ በአንድ ትውልድ ተሠርቶ የሚጠናቀቅ አይደለም፤ ይህ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚዘልቀውን የቤተ ክርስቲያን ሥራ በአጥጋቢ ሁኔታ ለማከናወን በየደረጃው የሚገኙ የሀብተ ክህነት አገልጋዮች እርስ በእርሳቸው በመደማመጥ መሥራት አለባቸው፤ የሚያገለግሉት ማኅበረሰብም በየጊዜው የሚያቀርብላቸውን ጥያቄ በሕጋዊ መንገድ በመቀበል በበሰለና በሰከነ አእምሮ መልስ ሊሰጡ ይገባል፡፡ ማንም ሰው ለምን ትጠይቃለህ አይባልም፤ ነገር ግን ጥያቄውን ተቀብሎ ከቅዱስ መጽሐፍ፣ ከሃይማኖት ድንጋጌ፣ ከሕገ ቤተ ክርስቲያንና ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጋር ያለው ግንኙነትና ልዩነት ምን ይመስላል? የሚለውን መርምሮና ተንትኖ በማብራራት ማስተዋልና ብስለት ያልተለየው፣ ኅሊናን የሚያሳምን በቂ መልስን መስጠት ይገባል፤ ቅዱስ ጴጥሮስመልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑያለውን መሪ ቃል ከቶውኑ ልንረሳው አይገባም፡፡ በትህትና፣ በመከባበርና ቅን የሆነ አስተሳሰብን በማራመድ፣ የሚደረገው ውይይት ምንጊዜም የችግር መፍትሔ ነው፤ ቤተ ክርስቲያናችን በዚሁ መሥመር ከተጓዘች የማትፈታው ችግር አይኖርም፡፡ ስለዚህ ሁላችንም ከእግዚአብሔር የተቀበልነውን የሀብተ ክህነት አገልግሎታችንን ጥበብና ማስተዋል ባልተለየው ብልሐት እየፈጸምን ኃላፊነታችንን መወጣት ይኖርብናል፤›› ብለዋል፡፡ 

 ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ ዜና ዕረፍታቸውን ተከትሎ ከአገር ውስጥና ከዓለም ዙሪያ የሐዘን መግለጫ እየጎረፈ ነው፡፡
ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ባስተላለፉት መግለጫ፣ “ለመላ ሰብዓዊ ፍጡራን ጥልቅ ፍቅር የነበራቸው እኒህ ታላቅ መንፈሳዊ መሪ መላ ሕይወታቸውን በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ደኅንነት እንዲሁም ለማኅበራዊ ሰላምና ኅብረት ታላቅ ጠቀሜታ ያላቸው አያሌ መንፈሳዊ አገልግሎቶችን በማበርከት አሳልፈዋል፤'' ብለዋል፡፡ የቅዱስነታቸው ብልህ መንፈሳዊ አመራር፣ የማያወላውል ጽናትና ጥልቅ ሰብዓዊ ርህራሄ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምዕመናን ዘንድ ብቻ ሳይሆን በመላ ዓለም በሚገኙ ሰላም ወዳድ ሕዝቦች ልብ ውስጥም ልዩ ስፍራ እንዲኖራቸው ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ 
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አባዱላ ገመዳ ‹‹ማጣት የማይገባንን አባት አጥተናል፤ እጅግ  የሚያሳዝን አስደንጋጭ ኀዘን ነው የሰማነው፤›› ሲሉ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን በበኩላቸው. ‹‹የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሞት ትልቅ ጉዳት ነው፤ ትልቅም ክፍተት ተደርጎ ሊታይ ይችላል፤›› ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የእስልምና፣ የካቶሊክና፣ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት መሪዎችም አክብሮታቸውንና ሐዘናቸውን የገለጹ ሲሆን፣ በተለይ የኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ ቄስ ዓለሙ ሼጣ፣ “በዓለምና በአፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ውስጥ ባላቸው መንፈሳዊ አመራር ባሳዩት ብቃት ለዛሬው መንፈሳዊ አባቶች ምሳሌነት ያለው መሠረትን ጥለዋል፤” ብለዋል፡፡ የሮማው ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት አቡነ ቤኒዲክት 16ኛም ለቤተ ክርስቲያኒቱ ባስተላለፉት የኀዘን መግለጫ በፓርትያርኩ ድንገተኛ ሞት ጥልቅ ኀዘን እንደተሰማቸው በቤተ ክርስቲያናቸው ስም ገልጸዋል። ለእምነቱ ተከታዮችም መጽናናትን ተመኝተዋል። 
“'ቅዱስነታቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነትና ወዳጅነት እንዲጠናከር ያደረጉት ጥረትም የሚደነቅ ነው፤'' ብለዋል። 
የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት በዋና ጸሐፊው ሪቨረንድ ዶ/ር ኦላቭ ቲበት በኩል በላከው መግለጫም፣ ‹‹ቅዱስነታቸው ለዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ያበረከቱት የላቀ አስተዋጽኦ ሁሌም የምንዘክረውና የማንረሳው ነው፤›› በማለት በሐዘን ስሜት ገልጸዋል፡፡

በሙሉ መጠርያቸው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቀነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት የነበሩት አቡነ ጳውሎስ ያረፉት ሐሙስ፣ ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ንጋት ላይ ነው፡፡
 የ76 ዓመቱ ፓትርያርክ የድንገተኛ ሕልፈታቸው መንስዔ የስኳር ሕመምና የደም ግፊት መሆኑንና በደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታል ማረፋቸውን የቤተ ክርስቲያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ይፋ አድርጓል፡፡ ባለፈው ዓርብ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረገው ቅዱስ ሲኖዶስ ባወጣው መግለጫ የፓትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር ሐሙስ ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም. በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በብሔራዊ ክብር ይፈጸማል፡፡ 


በረከታቸው ይደርብን
ነፍሳቸውን በአብርሃም እና በይስሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን

ዋቢ ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

14 comments:

  1. ገብረ ማርያም ዘጎንደርAugust 20, 2012 at 11:19 AM

    አሜን በረከታቸው ይደርብን ነፍሳቸውን በአብርሃም እና በይስሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን!

    ReplyDelete
  2. GOD bless you Mele! Egziabher nebsachewun yimar!

    ReplyDelete
  3. አሜን በረከታቸው ይደርብን

    ReplyDelete
  4. Dn Melaku

    Thank you very much.

    ReplyDelete
  5. I wish if I can use the Amharic font and write what I feel from the bottom of my heart. Anyways;

    May the Almighty God bless you in abundance of wisdom and grace. What a real and appropriate profile is it. I am highly touched and greatly satisfied with the contents. Ofcourse this Holy father has a lot more done than what we can write in this small page. But in a nut shell, this is great and concise to reveal to the public.

    God bless you.


    አሜን በረከታቸው ይደርብን: ነፍሳቸውን በአብርሃም እና በይስሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን!

    ReplyDelete
  6. በውነት እግዚአብሔር ይባርክህ ወንድሜ!
    ስለሳቸው እስከዛሬ ሰምቼ የማላውቀውን ነው ያነበብኩት።
    ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳትሆን አገርም የሚትኮራባቸው አባት ነበሩ ማለት ይቻላል።
    በዚህ ወቅት ልንሰማውና ልናውቀው የሚገባን ይህንና ይህን የመሰለውን ነበር።
    አሜን በረከታቸው ይደርብን።
    ነፍሳቸውን ከቅዱሳን ጉባዔ ይደምርልን።

    ReplyDelete
  7. ስማቸውን በበጎ ጎኑ የነገረን ሰው የለም ነበር እስከዛሬ ድረስ፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ አሜን በረከታቸው ይደርብን፡፡

    ReplyDelete
  8. "ስማቸውን በበጎ ጎኑ የነገረን ሰው የለም ነበር እስከዛሬ ድረስ፡፡"

    እውነት ነው እኔም እስከዛሬ ስለሳቸው ከደጀ ሰላምና ከአንድ አድርገን ስሰማ የኖርኩት ኃጢአታቸውን ብቻ ነበር።

    እንዲህም ዓይነት ሰው ነበሩ ለካ።

    እግዚአብሔር ይስጥልን

    በዚህ ወቅት ልንሰማውና ልናውቀው የሚገባን ይህንና ይህን የመሰለውን ነበር።
    አሜን በረከታቸው ይደርብን።
    ነፍሳቸውን ከቅዱሳን ጉባዔ ይደምርልን።

    ReplyDelete
  9. Thank you very much Melaku:

    ReplyDelete
  10. ክቡራን ስንክሳሮች ስለቅዱስነታቸው መልካም ጽፋችኋል፡፡ ግን ለምን ጽሑፉን ያገኛችሁበትን ሪፖርተር ጋዜጣን መጻፍን ዘንግታችኋልና አስገቡት፡፡
    ኃይለ ገብርኤል ዘማኅበረ ክርስቶስ

    ReplyDelete
  11. ስለ ቅዱስነታቸው መጻፋችሁ ጥሩ ሆኖ ሳለ ጽሑፉን ያገኛችሁበትን ምንጭ ሪፖርተር ጋዜጣ (የነኃሴ 13 ቀን 2004 ዓ.ም. እትም) አለመጥቀሳችሁ ዘንግታችሁ ነው ወይስ? . . .

    ReplyDelete
  12. አሜን በረከታቸው ይደርብን ነፍሳቸውን በአብርሃም እና በይስሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን!

    ReplyDelete
  13. ውድ ዲ/ን መላኩ፡- ከሁሉ አስቀድሜ ዘወትር ለምታደርሰን መንፈሳዊ መረጃ እያመሰገንኩ ጽሑፉ ውስጥ በግልጽ ስላልተካተተ አንድ ጉዳይ ጥያቄ ላነሳ እወዳለሁ፡፡
    በጽሑፉ ውስጥ “ ከብፁዓን ወቅዱሳን አቡነ ባስልዮስና አቡነ ቴዎፍሎስ፣ አቡነ ተክለሃይማኖትና አቡነ መርቆሬዎስ በኋላ አምስተኛው (5ተኛው) ፓትርያርከ ሆነው የመጡት አቡነ ጳውሎስ…” ይላል፡፡ ታዲያ አቡነ ጳውሎስ ከአቡነ መርቆሪዎስ በኃላ እንዴት እንደተተኩ በግልጽ ያልተቀመጠው ለምንድን ነው? አሁንም ቢሆን ስለዚህ ጥያቄ ግልጽ መረጃ ካለህ ብትጽፍልን? እግዚአብሄር ሀገራችንን ይባርክ! ለቤተክርስትያናችንም ጥሩ አባት ያስቀምጥላት!

    ReplyDelete
  14. Thanks you have said a lot about our father Abune Paulos,May God rest his sol with Abrahm, Isaac and Jacob.I have heard so many wonderful things that our father done during his life time.and we also know as Ehiopian Orthodox Christian memen ዲያቆን መልአኩ እዘዘው Bible says '' say the truth is the truth and lie is lie'' Why did you afriad to say the scare that Abune Paulos left on Ethiopian Orthodox chuch which is the darkest time in history of Church.As the head of the Ethiopian Orthodox church, Abune Paulos could have done.Where was he? When about 16 chuches burnt down in Welaita Sodo,the Masacre of Jimma Semae'tat,and in its history the Ethiopian Orthodox church dived in to Three parts in personal glory rather than the God's glory? how many churches burned to ashes and how many christians are slaughtered during Abune Pauos time? It was the resent memory that the Addis Ababa univerist was hand overd for masacre when they shelterd in the Church compound. and how many papasat door was broken because of they oppose the ruining plan of Aba Paulose?.Abune Paulos killed the Ethiopian Orthodox church for the generation to come,eveyone knows evenif you didn't want or the part of the ruin. As you are Decon,Please speak and tell people the truth and We expect from you a lot you are one of the Hariyat, and you should not based on the lie. If you want to say about someone say all about that person, whether it is good or bad the history will judge. I am so sorry to hear from you the Deconn just one sided. I hope that you may not condem me because of I say the truth.
    God of Abrham may strengthen you just like Metimiku Yohannes who did not frea to speak the trueth and gave his live for the true words of God.

    ReplyDelete