Friday, May 4, 2012

የቅዱሳን መሰወር (ኅብአተ ቅዱሳን) -ክፍል 1


ዮሐንስ ወንጌላዊ

የሰው ልጆች ወደ እግዚአብሔር በመንፈሳዊ አገልግሎት ባዘነበሉ መጠን ቸርነት የባሕርዩ የሆነ እግዚአብሔር ደግሞ የተለያየ መንፈሳዊ ብቃትን ይሰጣቸዋል፤ ሰማያዊ ምሥጢርን ይገልጥላቸዋል። ቅዱሳን በሥጋቸው በምድር ለጸሎት ቆመው ነፍሳቸው በተመስጦ ገነት መንግሥተ ሰማያት ተነጥቃ ሄዳ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ታመሰግናለች። እንዲሁም በአካል እንደ ነቢያቱ ሄኖክና ኤልያስ በመወሰድ እስከ ጌታችን ዳግም ምጽአት መዳረሻ ቀን በመሰወር እንደሚኖሩ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል።

«መሰወር» የሚለው ቃል የግእዝ ግሱ «ኀብአ»፦ «ሰወረ፥ መሰወር»፤ «ተኀብአ»፦ «ተደበቀ፥ ተሰወረ፥ ራቀ፥ ረቀቀ» ማለት ሲሆን በጥቅሉ ለዓይን እንዳይታይ እንዳይገኝ ሆነ፤ ለምሥጢርም ከሆነ ለአእምሮ ረቀቀ ማለት ነው ።

«መሰወርን» የምንዳስስበት ሃይማኖታዊ ጠገግ ወይም አድማስ በሥጋ ለባሽነት የኖሩትን የሰው ልጆችን በጽድቅና በቅድስና መሰወር የሚያካትት ነው። በዚህም መሠረት ከሰው ልጆች ወገን፦ በቅድስናቸው ብቃት፥ እግዚአብሔር በሰጣቸው ጸጋ እስከ ምጽአት ድረስ በሥጋቸው በብሔረ ሕያዋን እንዲሰወሩ፤ ከሰው ልጆች ዓይን ለጊዜው ለአስፈላጊ ሁኔታ እንዲሰወሩ፤ ከመደበኛ መልካቸው ለጊዜው ሌላ ሰው በመምሰል እንዲሰወሩ፤ መከራ እንዳያገኛቸው የሰወራቸውና ከሞቱ በኋላ ቅዱስ ሥጋቸውን የሰው ልጆች እንዳይቀብሯቸው የተሰወሩት ወዘተ ይገኙባቸዋል።


እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት አንድ ሰው ለመሰወር የተለያዩ የብቃት ደረጃዎች ላይ መድረስ አለበት። ደረጃዎቹም ሊገኙ የሚችሉት ሃይማኖትን ከምግባር ጋር በማጽናት፣ በጾም፣ በጸሎትና በትሩፋት ማጌጥን ይጠይቃል። የብቃት መዓርጋቱም በሦስት ዐበይት መዓርጋትና በዐሥር ንዑሳን ደረጃዎች ይከፈላሉ። የመጀመሪያው ዐቢይ መዓርግ ንጽሐ ሥጋ ይባላል። በውስጡም ጽማዌ፣ ልባዌና ጣዕመ ዝማሬን ያጠቃልላል። «ጽማዌ»፦ ከአንደበት ከሚወጣ ኃጢአት መቆጠብና ንግግር አለማብዛት፤ «ልባዌ»፦ ፍጹም መንፈሳዊ እና እውነት የሆነውን ነገር በሚገባ ማስተዋል፤ «ጣዕመ ዝማሬ»፦ የእግዚአብሔርን ምሥጢር በንቃትና በተመስጦ ሆኖ በዜማ ላህይ በማመስገን መትጋት ነው።

ሁለተኛው ዐበይት የብቃት መዓርግ ንጽሐ ነፍስ ነው። ቅዱሳን ወደዚህ መዓርግ የሚደርሱት የመጀመሪያውን ሲያልፉ ነው።

በውስጡም አንብእ፣ ኩነኔ፣ ፍቅርና ሁሰትን ያጠቃልላል። «አንብእ» ከመንፈሳዊ ተመስጦ የተነሳ እንደምንጭ /ሰን ውኃ/ ከቅዱሳን ዓይን እንባ የሚፈስበት ደረጃ ነው። «ኩነኔ» ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ በመንፈሳዊ ጥበብ የማስገዛት ደረጃ ነው። «ፍቅር» በቅዱሳኑ ዘንድ የሰው ልጆችን ዘር ሁሉ እኩል የመውደድ ደረጃ ነው። «ሁሰት» በዚህ ደረጃ ቅዱሳኑ በቅርብም በሩቅም ማንኛውንም ክንውን በዓይነ ሥጋ ሳይሆን በዓይነ መንፈስ ማየት ነው። ይህም የቅዱሳን መላእክትን እንቅስቃሴ /ተልእኮ/ እስከማወቅ ያደርሳቸዋል።

ሦሰተኛው ዐቢይ የብቃት መዓርግ ንጽሐ ልቡና ነው ። ይህ የመጨረሻው የፍጹምነት ደረጃ ነው ። በውስጡም ንጻሬ መላእክት፣ ተሰጥሞ ብርሃን፣ ከዊነ እሳት ይገኙበታል። «ንጻሬ መላእክት» በዓይነ ሥጋ ቅዱሳን መላእክትን በያሉበት ዓለማት መመልከት ነው። «ተሰጥሞ ብርሃን» በእግዚአብሔር ልዩ የባሕርዩ ብርሃን መመሰጥ ሲሆን «ከዊነ እሳት» ደግሞ ቅዱሳን ሰዎች በእሳታዊነት ጸጋ ከነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ የሚደርሱበት ደረጃ ነው።

ከላይ እንዳየነው በእነዚህ የብቃት መዓርጋት ውስጥ ያሉ ቅዱሳን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ከሚሰጧቸው ጸጋዎች አንዱ መሰወር ነው። የመሰወር ጸጋውም የተለያዩ ሁኔታዎች አሉት። እንደሚከተለው እንመለከተዋለን።

፩. በሕይወተ ሥጋ ሳሉ ለጊዜው መሰወር 

ይህ የመሰወር ጸጋ በዓለመ ሥጋ መካከል ሳሉ አስፈላጊ ለሆነ ሁኔታ አብረው ካሉት ሰው ለጊዜውም ቢሆን አለመታየት ነው። ይህን ዓይነት መሰወር በጾም በጸሎት ተወስነው፥ በብሕትውና ያሉ ቅዱሳን ከፈቃደ እግዚአብሔር ውጪ ሊያዩአቸው የሚመጡትን ሰዎችና በክፉ የሚመጡባቸው ሰዎች እንዳያገኟቸው የተሰጣቸው የመሰወር ጸጋ ነው። ይህንንም እውነታ ለቅዱሳኑ ማድረግ እንደሚቻላቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል። ለዚህም አብነት የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። በግእዙ «ወዘንተ ብሂሎ እግዚእ ኢየሱስ ሖረ ወተኃብኦሙ»፤ ትርጉሙም፦ «ኢየሱስ ይህን ተናግሮ ሄደና ተሰወረባቸው።» /ዮሐ. ፲፪፥፴፮፤ ሉቃ. ፳፬፥፴፩/። ከላይ ያለውን ንባብ ስንመረምር ጌታችን ሲያስተምር በጊዜው በጉባኤው ላይ የተገኙት አይሁድ ትምህርቱን በመቃወም ሊገድሉት ፈልገው፥ ሊይዙት ነበር። ጌታችን ግን ራሱን አሳልፎ የሚሰጥበት ጊዜ ስላልደረሰ ከአጠገባቸው እያለ ተሰወረባቸው ። በአጠገባቸው አልፎ በመካከላቸው ሲሄድ ማየት እንዲሳናቸው አደረጋቸው። 

ለቅዱሳኑም ይህን ጸጋ ሰጥቷቸዋል። በእነርሱ አድሮባቸው ይኖራልና ይሰወራሉ። «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል።» /ዮሐ. ፲፬፥፲፪/። በግብረ ሐዋርያት መጽሐፍ ላይ ይህን ታላቅ ተአምር በተግባር እናየዋለን። ሄሮድስ በቤተ ክርስቲያን ላይ መከራ ባጸናባት ዘመን የዮሐንስ ወንድም ቅዱስ ያዕቆብን በሰይፍ በማስገደል፤ አይሁድን ይበልጥ ደስ ለማሰኘት ቅዱስ ጴጥሮስን ከፋሲካ በኋላ ሊያወጣላቸው ሌሊትና ቀን ቆመው በሚጠብቁት ወታደሮች አስከበበው። ነገር ግን በቤተ ክርስቲያን ሰለ እርሱ አጥብቆ ይጸለይ ነበር። ሄሮድስ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳያመልጥ ፈጽሞ ስለፈለገ በሁለት ሠንሠለት ታስሮ በሁለት ወታደሮች መካከል እንዲተኛ አስደረገ። በተጨማሪም በሩ እንዳይከፈት ጠባቂዎችም በደጁ ፊት ሆነው በተጠንቀቅ ይጠብቁ ነበር። ቅዱስ ጴጥሮስን ሊያወጣው በመጣው የእግዚአብሔር መልአክ አማካይነት ተቀስቅሶ ከሁለቱ ጠባቂዎች መካከል ሲነሣ ያየው ጠባቂ የለም። ሠንሠለቶቹ ከእጆቹ ሲወልቁና ሲወድቁ ያስተዋለው አልነበረም። በተለይ የሚገርመው በሩን በተጠንቀቅ ደጁ ላይ ሆነው ይጠብቁ የነበሩ ጠባቂዎች በሩ ተከፍቶ ቅዱስ ጴጥሮስ ሲወጣ ሊያዩት አልቻሉም። ምክንያቱም ከእርሱ ጋር ያለች የእግዚአብሔር የመሰወሪያው ጸጋ ጠብቃዋለችና ነው። የእግዚአብሔር መልአክ ባለበት የእግዚአብሔር ቸርነት አለና። ሲነጋም ወታደሮቹ ቅዱስ ጴጥሮስን «ምን ነካው? ወዴት ጠፋ?» ብለው ታወኩ። ምክንያቱም በሩ ሳይከፈትለት፥ በቁልፉ እንደተቆለፈ ሆኖ ወታደሮች በተጠንቀቅ ሳሉ ወዴት ሄደ ይበሉ? እነርሱ አላወቁም እንጂ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርን በጸሎት ትማፀን ስለነበር የእግዚአብሔር መልአክ ለሞት ከጠበቁት ወታደሮች ዓይን ሰውሮ አውጥቶታል። ወዲያውም ወደ ማርቆስ እናት ቤት በመሄድ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ ነግሯቸዋል። ከዚህም እግዚአብሔር በፈለገ ጊዜ እንደወደደ ቅዱሳኑን ለጊዜውም ቢሆን የመሰወር ብቃት እንደሚሰጣቸው እንረዳለን። /የሐዋ. ፲፪፥፮-፲፱/።

፪. የመገለጥ ጊዜ እስኪደርስ ሌላ ሰው በመምሰል መሰወር

ለዚህም ምሳሌ የምናደርገው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ነው። በትንሣኤው ዕለት በመቃብሩ የተገኘችው መግደላዊት ማርያም ዘወር ብላ ጌታችንን አይታው ነበር። ነገር ግን አላወቀችውም። እንደውም የአትክልት ጠባቂ መስሏት ነበር። ፈቃዱ እስኪሆንም ልታውቀው አልቻለችም። ከጭንቀቷ የተነሣ «ወዴት እንዳኖርከው ንገረኝ» በማለት ራሱን ትጠይቀው ነበር። ፈቃዱ በሆነ ሰዓት «ማርያም» ብሎ በመጥራት እንድታውቀው አደረጋት። /ዮሐ. ፪፥፲፩-፲፯/።

የኤማሁስ ሰዎችም ታሪክ ተመሳሳይ ሁኔታን የያዘ ነው። ስድሳ ምዕራፍ ቀኑን ሙሉ እስከምሽት ቃሉን እየሰሙ ፊቱን እያዩ ቢጓዙ በፈቃዱ እርሱን ለማየት እንዲበቁ እንጀራ ቆርሶ እስኪሰጣቸው ሊያውቁት አልቻሉም። በዓይናቸው ፊት እያዩት ሳለ እርሱ መሆኑ ተሰውሮባቸው ነበር። «ቆርሶ ሲሰጣቸው ዓይናቸው ተከፈተ። ዐወቁትም። ወዲያውም ከዓይናቸው ተሰወረ።» /ሉቃ. ፳፬፥፲፫-፴፭/። ጌታ ለወደደው በወደደው ጊዜ ይገለጣል፤ ለሌላው ይሰወራል። በአንድ ጊዜና እይታ ሳሉም የሰዎችን የተሰወረውን የማወቅን ብቃት ይለያያል። ይህንንም በጥብርያዶስ ባህር ዓሣ በማጥመድ ላይ ያደሩ ሐዋርያት ታሪክ በሚገባ ያስረዳናል። ሲነጋም «ጌታ እኮ ነው» በማለት ለቅዱስ ጴጥሮስ ሲነግረው ሊረዳ ችሏል። በኋላም በየደረጃው ሁሉም ሐዋርያት ሊያውቁት ችለዋል። /ዮሐ. ፳፩፥፬-፲፬፤ ፩ኛ ሳሙ. ፫፥፩-፲፬/።

ለሰው ልጆችም እንደብቃታቸው መጠን ይህች ጸጋ ተሰጥታቸዋለች። ነቢዩ ኤልሳዕ ከሩቅ በሶርያ ቤተ መንግሥት የሚደረገውን በጸጋ እግዚአብሔር የማወቅ ደረጃ ደርሶ ነበርና የሶርያ ንጉሥ የመከረውንና ያቀደውን እያወቀ ለእስራኤል ንጉሥ ይነግረውና እስራኤልን ከአደጋ ይጠብቅ ነበር። የሶርያ ንጉሥ ይህን ባወቀ ጊዜ ጭፍሮቹን ልኮ ነቢዩ ኤልሳዕን እንዲይዙት አስከበበው። ነቢዩ ኤልሳዕም የሶርያ ጭፍሮች ዓይኖች እርሱ ያለበትን ቦታ እንዳያውቁት፥ ዓይነ ስውርም እንዲሆኑ ጸለየ። እግዚአብሔርም የነቢዩ ኤልሳዕን ጸሎት ሰማ። ነቢዩ ኤልሳዕም እንደሌላ ሰው እንዲመስላቸው አደረገ። ነቢዩ ኤልሳዕም እንደሌላ ሰው ሆኖ «ኤልሳዕ ያለበትን ቦታ ላሳያችሁ» ብሎ ወደ ሰማርያ ወሰዳቸው። እንደገናም «ዓይኖቻቸውንም ግለጥ» በማለት ጸለየና በሰማርያ መካከል መሆናቸውንና መርቶ ያመጣቸው ነቢዩ ኤልሳዕ መሆኑን እንዲለዩ አደረጋቸው። እዚህ ላይ ነቢዩ ኤልሳዕ የበቃ ሰው በመሆኑ በጸሎቱ የሶርያ ወታደሮቹን እየመራቸው ሲመጣ እርሱ እንደሆነ እንዳያውቁት፥ ያለበትንም ቦታ እንዳይለዩ አደረጋቸው። ይህም የእርሱ ማንነት እንዲሰወራቸው በመኾኑ ነው።
እንደዚሁም ጻድቁ ገብረ ክርስቶስ ከሙሽርነቱ ቦታ በእግዚአብሔር ተጠርቶ ከቤተሰቦቹ በተለየ ጊዜ የአባቱ ጭፍሮች እርሱን በፍለጋ እንዳያገኙ ሰውነቱ እንዲለወጥ ጸለየ። እግዚአብሔርም እርሱ እንደሆነ እንዳይታወቅ በቁስል ሸፈነው። በዚህም ሁለት ነገር እንዲያገኝበት አድርጎታል። አንደኛው ከቤተሰቦቹ እንዲሰወር ሁለተኛው በመከራው ዋጋ እንዲያገኝበት የእግዚአብሔር ሙሽራው ሆኗልና። ዐሥራ አምስት ዓመት በሰው አገር፣ ዐሥራ አምስት ዓመት በአባቱ ደጅ ሲተኛ ያወቀው የለም። እዚህ ላይ መረዳት ያለብን ምንም እንኳ በቁስል ቢመታ በአንድ ምልክት ቤተሰቦቹ ሊያገኙት ይችሉ ነበር። የእግዚአብሔር ጸጋው ሸፍናዋለችና ይህን ያህል ዓመት በደጃቸው ሆኖ ተሰውሯቸው ኖሯል።

፫. ልዩ መሰወር

እስራኤላውያን እግዚአብሔርን በመበዳላቸውና ከኃጢአታቸው አልመለስ በማለታቸው፣ ለባቢሎናውያን አሳልፎ ሰጣቸው። በመካከላቸው ግን ከነቢዩ ኤርምያስ ጋር ለእስራኤል ሕዝብ መልካም ያደርጉና ለእግዚአብሔር ታዛዦች የሆኑ «የኢየሩሳሌምን ጥፋት አታሳየን» ይሉ የነበሩ ነቢዩ ባሮክና ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክን ከመከራና ከግዞት እግዚአብሔር እንደሰወራቸው እንመለከታለን። ይህ እንዲሆን ነቢዩ ኤርምያስ ወደ እግዚአብሔር ስለ ሦስት ነገር በጸሎቱ አመለከተ። በመጀመሪያ ስለንዋያተ ቅዱሳቱ መሰወር እንዲህ ብሏል «አቤቱ ጌታዬ፥ ይህችን አገር በጠላት እጅ አሳልፈህ እንድትሰጣት የባቢሎን ወገኖች እንዲይዟት እነሆ ዛሬ አወቅሁ። ...ስለምናገለግልበት ንዋያተ ቅዱሳት ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?» ጌታም «እርሱን ወስደህ ለምድር በቤተ መቅደስ አደራ ስጣት፤ አንቺ ምድር በውሆች ላይ የፈጠረሽ የሰገነት ክፍልም የከፈለሽ የፈጣሪሽ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተሽ፥ ጌጥሽን ተቀበይ፤ ዘሩባቤል እስኪመጣ ድረስ ገንዘብሽን አደራ ጠብቂ በላት» አለው። ባሮክና ኤርምያስ ወደ ቤተ መቅደስ ገቡ፤ የሚያገለግሉበትን ዕቃ ሁሉ ጌታ እንዳዘዛቸው ለምድር ሰጧት። ምድርም ያን ጊዜ አደራ ተቀብላ ዋጠች። ይህም ምድር የቤተ መቅደሱን ንዋያተ ቅዱሳት መሰወሯን፥ መደበቋንና መሸሸጓን ያመለክታል።

ሁለተኛም «…ለኢትዮጵያዊው ሰው ለአቤሜሌክ የማደርገውን ግለጥልኝ፤ ...እርሱ ከረግረግ ጉድጓድ ውስጥ አወጣኝ፤ እንዳያዝን የአገሪቱን ጥፋት ያይ ዘንድ አልወድለትም» በማለት ጸለየ። ጌታም ለኤርምያስ «ወደ አግሪጳ የወይን ቦታ በዚህ ተራራ ጎዳና አቤሜሌክን ላከው፤ ሕዝቡን ወደ አገራቸው እስክመልሳቸው ድረስ እኔ እሰውረዋለሁ።» አለ። በነጋውም ኤርምያስ እግዚአብሔር እንዳዘዘው አቤሜሌክን እንዲህ ብሎ አዘዘው «ወደ አግሪጳ የወይን ቦታ ለታመሙ ወገኖች ትንሽ በለስን አምጣ ብሎ ላከው። …አቤሜሌክም ኤርምያስ ከላከው ቦታ በቀትር ጊዜ በለሱን አመጣ፤ ጽፍቅ ያለች ዱርንም አገኘ፤ ጥቂትም ያርፍ ዘንድ በጥላዋ ሥር ተቀመጠ፤ በለስ ያለባትን ሙዳይ ተንተርሶ ስድሳ ስድስት ዓመት ተኛ። ሲነቃም «ገና ራሴን ይከብደኛል፤ እንቅልፌን አልጨረስኩምና ዳግመኛ ጥቂት ብተኛ በጎ ነገር ነው» አለ። ያን ጊዜም በለስ ያለበትን ሙዳይ ከፈተ በለሶችም በሙዳዩ ውስጥ አዲስ ሆነው ወተታቸውም ሲፈስ አገኘ። «ተመልሼ እንዳልተኛ እንዳልዘገይም አባቴ ኤርምያስ እንዳይነቅፈኝ እፈራለሁ» አለ። ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ሲገባ አገሩን ሊያውቀው አልቻለም በስድሳ ስድስቱ ዘመን ዛፎች በቅለው ደን ሆኖ ነበርና።

ሦስተኛም እግዚአብሔር ለነቢዩ ኤርምያስ «ባሮክን ግን በኢየሩሳሌም ተወው አለው» ባሮክም ስድሳ ስድስቱን ዘመን በመቃብሩ ስፍራ ባለው የመቃብር ቤት ተሰውሮ አሳለፈ። ዘመኑም ከተፈጸመ በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ አቤሜሌክን ወደ ባሮክ መርቶ ወሰደው። ባሮክም በመቃብር ቤት ተቀምጦ ነበር።» /ትንቢተ ኤር. ፴፱፥፲፭-፲፰፤ ተረፈ ባሮክ ፪፥፭-፲፫፣ ፫፥፩-፲፫፣ ፬፥፪/ በማለት የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል። ከአቤሜሌክ ተአምራዊ እንቅልፍ ምን እንረዳለን? «እግዚአብሔር እሰውረዋለሁ» እንዳለ ከጠላቶች ሰውሮታል።

የሚገርመው ነገር አቤሜሌክ ራሱ ከራሱ ተሰውሮበታል። ስድሳ ስድስት ዘመን እንደ ጥቂት ደቂቃ አሳልፎ በመነሳቱ ከስድሳ ስድስቱ ዘመንም /ከጊዜ/ ተሰውሯል። የተኛው ጫካ ውስጥ ነበር፤ ከአውሬ፣ ከዝናብ፣ ከብርድ፣ ከፀሐይ ወዘተ ተሰውሯል። በላዩ ላይ ሣር በቅሎበት አልጠፋም። የእግዚአብሔር ተአምራዊ ጸጋው ከጥፋት ሰውራዋለች። «ወሰወረኒ በምኀባአ ጽላሎተ» ትርጉሙም «በድንኳኑም መሸሸጊያ ሸሽጎኛልና» እንዳለ ቅዱስ ዳዊት። /መዝ. ፳፮፥፭/።
ስለ ብሔረ ብፁዓን ፤ ደብር ቅዱስ ፤ብሔረ ሕያዋን በሚቀጥለው ክፍል እንመለከታለን
እግዚአብሔር ምስጢሩን ይግለጽልን

ይቆየን

15 comments:

  1. ቃለ ሂዎት ያሰማልን ባለፈው የህማማት ሰሞን ተሰውረው ስለነበሩት ልጆች እስኪ የተወሰነ ነገር ይንገሩን የተከበሩ ወንድማችን ኢንጅነር ዲያቆን መላኩ

    ReplyDelete
  2. KALE HIWOT YASEMALIN!
    BETAM ASTEMARI TSIHIF NEW.

    ReplyDelete
  3. kale heiwate yasamalen

    ReplyDelete
  4. ቃለ ሂዎት ያሰማልን::መድኋኔዓለም የጀመርከውን ያስጨርስህ:: ለኛ በስደት ላለነው ደግሞ በሩቅ ሁነን ከማንበብ ቀርበን ለመማር የድንግል ልጅ ይርዳን:: አሜን

    ReplyDelete
  5. kale hiwot yasmalign

    ReplyDelete
  6. Ejig...Ejig Betam Dess yemil..yemiyareka...yemiyastemir yehiywot kal!<<< E/R Bekidusanu Dinik new!>>>+++kalehiywot yasemalin Menigistun ena tsidikun yawursilin!

    ReplyDelete
  7. beahunu zemen ABATACHEN CHERU AMLAKACHEN bemdrachen lay ende abimelik yale sadeq fetur ysnsalen AMEN!!! qaleh hiywet yasemalen.

    ReplyDelete
  8. qale heyewete yasemalen,beheyewet betena yetebeqelen

    ReplyDelete
  9. egzihabhere kaleiwot yasemlne!

    ReplyDelete
  10. egziabher yistelen, rekik yehone temhert new:: betam be agramot anbebewalehu::

    ReplyDelete
  11. ወንድማችን ለዘመናት በውስጤ ጥያቄ የሆነብኝን መልስ አግቻለው እግዚአብሔር ያቆይልን በርታ::

    ReplyDelete
  12. ወንድማችን በርታ ለዘመናት በውስጤ ጥያቄ የሆነብኝን መልስ አግቻለው እግዚአብሔር ያቆይልን በርታ::

    ReplyDelete
  13. ወንድማችን በርታ ለዘመናት በውስጤ ጥያቄ የሆነብኝን መልስ አግቻለው እግዚአብሔር ያቆይልን በርታ::

    ReplyDelete
  14. kale hiwot yasemalen!

    ReplyDelete
  15. ቃለ ህይወት ያሰማልን!

    ReplyDelete