Thursday, April 19, 2012

ፋሲካ - የፋሲካ በግ - ትንሣኤ



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን፡፡
 በዲ/ ብርሃኑ አድማስ
እሥራኤልን ከግብጽ እየመራ የወጣው ሙሴ ሕዝቡን ከግብጽ ይዞ መውጣት ይቻለው ዘንድ የታዘዘው ታላቁ ትእዛዝ ፋሲካን በግብጽ ማክበር ነበር፡፡ ፋሲካ የሚባል በዓል ከዚያ በፊት ኖሮም ተከብሮም አያውቅም ነበርና በዝርዝር ማድረግ የሚገባቸዉ ሁሉ ተነገራቸዉ፡፡ ቀኑ በእነርሱ አቆጣጠር በአቢብ ወር በዐሥራ አራተኛዉ ቀን ይከበራል፡፡ ነውር የሌለበት የአንድ ዓመት ጠቦት በግ  ይመርጣሉ፡፡ በምድረ በዳ ሲመሽ ያርዱታል፡፡ ደሙን ወስደዉ የቤታቸዉን በር ሁለት መቃኖችና ጉበኑን ይረጩታል፡፡ ሥጋውን በሌሊት በእሳት ጠብሰው ይበሉለታል፡፡ ጥሬውንና በውኃ የተቀቀለዉን አይበሉም፡፡ የተረፈውን ሌሊቱን በእሳት ያቃጥሉታል፡፡በፍጥነት ይበሉታል፡፡ ከዚያ በኋላ ለሰባት ቀን የቂጣ በዓሉን ያደርጋሉ፡፡ ቂጣዉም ምንም እርሾ ያልገባበት ይሆናል፤ …./ዘፍ 12 1-36/፡፡

 ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ብዙ ዓይነት መሥዋዕት ሥርዓቶችና የበዓላት አከባበሮችን ተቀበሉ፡፡ በዚሁም መሠረት በየዕለቱ በጧት አንድ በማታ አንድ ነውር የሌለበት የበግ ጠቦት ይሠዋል፡፡ በየዕለቱም የእህል ቁርባን ይቀርባል፡፡በሰንበት፣ በወር መባቻና በሌሎች በዓላት ደግሞ የበጉ ቁጥር ይጨምራል፤ የፍየልና የከብት መሥዋዕቶችም ተጨምረዉ ይቀርባሉ፤ የእህሉም ቁርባን እንዲሁ፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ ሕዝቡ በበደሉ ጊዜ እንደ ኃጢኣታቸዉና በደላቸዉ መጠን የተለያዩ መሥዋዕቶችን ያቀርቡ ነበር፡፡በዘመነ ኦሪት ይህ ሁሉ ነገር በሥርዓት ጸንቶ ከዓመት እስከ ዓመት በዚህ መንገድ ሲፈጸም ኖሯል፡፡
የአይሁድ ፋሲካ በእነርሱ የአቢብ ወር በወሩ በዐሥራ አራተኛዉ ቀን እንዲከበር የታዘዘ በዓል ነዉ፡፡ ይህም የሆነበት የራሱ ምክንያት እንዳለዉ ሊቃውንት አስረድተዋል፡፡ በመጀመሪያ ወሩን የዐመቱ መጀመሪያ ወር ይሁናችሁ ብሏቸዋል /ዘጸ 122/፡፡ ይህንንም ይዘዉ ሊቃውንቱ መጀመሪያ ያለው ጥንተ ፍጥረት በዚህ ወር ቢገኝ ነዉ፤ ወይም ፍጥረትን የጀመረዉ (ጊዜንም ጭምር ማለት ነዉ) በዚህ ወቅት ነዉ ብለዉ ያስተምራሉ፡፡ በእኛ ቤተ ክርስቲያንም ይህ ትምህርት በትርጓሜ ሲሰጥ የኖረ ነዉ፡፡ በተለይም ጌታ ዓለሙን ለማዳን ሰዉ የሆነበት ጽንሰቱ መጋቢት 29 ቀን መሆኑንና በኋላም ጥንተ ስቅለቱን መጋቢት 27 አርብ አድርጎ ትንሣኤዉን እሑድ መጋቢት 29 ደግሞ ማድረጉ የዓለሙ ድኅነቱ የተፈጸመበት በዚህ ዕለት የሆነዉ ፍጥረቱን እም ኀበ አልቦ (ካለመኖር) ኀበ (ወደ መኖር) ያመጣዉ በዚህ ዕለት ስለሆነ ነዉ በማለት ያስተምራሉ፡፡
ከዚህም ተነሥተዉ ዓለም በዚህ ዕለት ተፈጥሮ በዚህ ዕለት ድኅነቱ እንደተፈጸመለት ሁሉ በኋላም በዳግም ምጽአት በዚሁ ዕለት መጋቢት 29 ቀን በዕለተ እሑድ በዘመነ ዮሐንስ ያሳልፈዋል ብለዉ ይጠብቃሉ፡፡ ነገር ግን በየትኛዉ ዓመት እንደሆነ እርሱ እንደ ተናገረዉ ማንም አያዉቅም ይሉናል፡፡ ለዚህ ነዉ በዘመነ ዮሐንስ የመጋቢት 29 በእሑድ መዋል አንዳንድ አባቶች ሲፈሩት የሚኖሩት፡፡ ስለዚህ ጌታ ለሙሴና ለእሥራኤል በግብጽ እያሉ ይህ ወር የዐመቱ መጀመሪያ ይሁናችሁ ያለዉ የፍጥረት መጀመሪያ ወር እንደሆነዉ የእናንተም ከግብጽ የምትወጡበት የመጀመሪያ ወር ይሁን ሲል፣ በዚሁ አንጻርም ደግሞ ነፍሳትም በግብጽ ከተመሰለች ከሲኦል በዚሁ ወር እንደሚወጡ ሲነግራቸዉ ነዉ፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ወደፊትም ዐለሙ አልፎ ጻድቃን መንግሥተ ሰማያትን ኃጥኣንም ገሃነመ እሳትን የምትጀምሩበት ይህ ወር እንደሆነ ዕወቁ ሲል ነዉ ይላሉ ሊቃውንቱ፡፡
የእኛ የትንሣኤ በዓልም በዚሁ ወር የሚከበርበት መሠረታዊ ምክንያትም ከዚሁ ጋር በተያያዘ ምክንያት ነዉ፡፡ ከላይ በሰፊዉ ለማተት እንደተሞከረዉ ጌታ የፋሲካዉን በግ ብሉ ያላቸዉ በወሩ በአሥራ አራተኛዉ ቀን ነዉ፡፡ ይህም የእነርሱ የወር አቆጣጠር በጨረቃ ስለሆነ ዐሥራ ዐራተኛዉ ቀን ማለት ጨረቃ ከተወለደችበት ወይም መታየት ከጀመረችበት ቀስ በቀስ እያደገች መጥታ ሙሉ የምትሆንበት ጊዜ ስለሆነ ነዉ፡፡ በሌላ ቋንቋ በሙሉ ጨረቃ ወይም በሙሉ ብርሃን ይሁን ማለቱ ነዉ፡፡ ይህም የፋሲካዉ በግ ቅዱስ ዮሐንስ የዓለምን ኃጢኣት የሚያስወግደዉ ያለዉ የክርስቶስ ምሳሌ ስለሆነ እርሱ እዉነተኛዉና ሕጸጽ(ጉድለት) የሌለበት ብርሃን መሆኑን አሁንም በምሳሌ ሲነግረን ነዉ፡፡ የሐዲስ ኪዳኗ ቤተ ክርስቲያናችንም በመንፈቀ ሌሊት ከገጠር እስከ ከተማ ያላትን ብርሃን ሁሉ አብርታ ምእመናኑንም በእጃቸዉ ጧፍ አስይዛ ‹‹ ትንሣኤከ ለእለ አመነ፣ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ፤ ትንሣኤህን ላመንን ለእኛ ብርሃንህን ላክልን›› እያለች በመዘመር መቅደሱን የምትዞረዉ ለዚህ ነዉ፡፡
 በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎ እንደምናገኘዉም መድኃኒታችን የተሰቀለዉ የአይሁድ የፋሲካ በዓል ሐሙስ ሆኖ አርቡን ነዉ፡፡ ያስታዉሱ፤ ጨረቃ ሙሉ ብርሃን በሆነችበት ዕለት ማለት ነዉ፡፡ በእርሱ ስቅለትም ይህችዉ ሙሉ ብርሃን የነበረች ጨረቃ ደም መሰለች፣ ሁልጊዜም ሙሉ የሆነችዉ ጸሐይም ጨለመች፣ ክዋክብትም ረገፉ፡፡ ሦስቱም በአንድነት አማናዊ ብርሃን እርሱ መሆኑን የእነርሱም ከእርሱ የተገኘ መሆኑን መሰከሩ፡፡ መድኃኒታችንም ድኅነታችን ፈጽሞ( ፍጹም አድርጎ) እሑድ ተነሣ፡፡ ስለዚህም ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የትንሣኤ በዓላችን የአይሁድ ፋሲካ ከዋለ በኋላ በሚዉለዉ እሑድ ማለትም እሥራኤል ከግብጽ ነፍሳትም ከሲኦል በወጡበት ወር ጨረቃም ሙሉ ብርሃን ከሆነች በኋላ በምሥጢር አጊጦ ያለፈዉን እያስታወሰ ብቻ ሳይሆን መጪዉን ዋናዉን ትንሣኤ ሙታንንም እያሳሰበ ሲዘከር ሲከበር ይኖራል፡፡በጨረቃ አቆጣጠር ወራቱ የሚውሉበት ጊዜ ስለሚለዋወጥ በሠላሳ አምስት ቀናት( ከመጋቢት 26 እስከ ሚያዚያ ሠላሳ ባለዉ ጊዜ) ዉስጥ ሁልጊዜም ከአይሁድ ፋሲካ በዓል በኋላ ባለዉ እሑድ ጥንተ ታሪኩንና ምስጢሩን እንደጠበቀ ሲከበር ይኖራል ማለት ነዉ፡፡
ለትንሣኤያችን ምሳሌ ሆኖ የቆየዉ ይኸዉ የፋሲካዉ በዓል መሥዋዕቱን በተመለከተም የራሱ ሕጎች ነበሩት፡፡ ‹‹እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን አለ። ይህ የፋሲካ ሕግ ነው ከእርሱ እንግዳ ሰው አይብላ። በብር የተገዛ ባሪያ ቢኖር ከተገረዘ በኋላ ከእርሱ ይብላ። መጻተኛና ሞያተኛ ግን ከእርሱ አይብሉ።በአንድ ቤትም ይበላ፤ ከሥጋውም አንዳች ከቤት ወደ ሜዳ አታውጡ አጥንትም አትስበሩበት። የእስራኤልም ጉባኤ ሁሉ ያድርጉት።እንግዳ ሰውም በመካከላችሁ ቢቀመጥ ለእግዚአብሔርም ፋሲካን ሊያደርግ ቢወድድ፥ አስቀድሞ ወንድ ሁሉ ይገረዝ፥ ከዚያም ወዲያ ይቅረብ፣ ያድርግ፣ እንደ አገር ልጅም ይሆናል፤ ያልተገረዘ ሁሉ ግን ከእርሱ አይብላ። ለአገር ልጅ በእናንተ መካከልም ለሚቀመጡ እንግዶች አንድ ሥርዓት ይሆናል። የእስራኤልም ልጆች ሁሉ እንዲህ አደረጉ፤ እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዳዘዘ እንዲሁ አደረጉ››/ዘጸ 12 43-50/ ተብሎ አንደተጻፈ ከላይ የተዘረዘሩት ሁሉ በሕግና በሥርዓት ይፈጽሙ ነበር፡፡
እነዚህ ሁሉ ግን ምሳሌዎች ነበሩ፡፡ እያዳንዱ ሰዉ ለኃጢኣትና ለበደል ከሚያቀርበዉ መሥዋዕት ጀምሮ ሁሉም ለሐዲስ ኪዳን አገልግሎታችንና መሥዋዕታችን ብዙ መልእክቶችን የተሸከሙ ነበሩ፡፡ ሐዋርያዉ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በግልጥ አይሁዳዊ የሆነ አይሁዳዊ አይደለምና፥ በግልጥ በሥጋ የሚደረግ መገረዝም መገረዝ አይደለምና›› /ሮሜ 228/ ሲል እንደ ገለጸዉ እነዚያ የመሥዋዕት ዓይነቶች ሁሉ ሌላ ትርጓሜ እንዳላቸዉ በቀላሉ መረዳት እንችላለን፡፡
የፋሲካዉ በግ ስለእኛ ስለሁላችን ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበዉ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነዉ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና›› /1 ቆሮ 5 7/ ሲል እንደ ገለጸዉ ፋሲካችን እርሱ ነዉ፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹ተጨነቀ ተሣቀየም አፉንም አልከፈተም ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም›› /ኢሳ 537/ ሲል የተናገረለት፣ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› /ዮሐ 1 29/ ሲል ያረጋገጠልን አማናዊዉ የፋሲካችን በግ እርሱ ነዉ፡፡
የፋሲካዉን በግ ደሙን የቀቡት ሁሉ ሞት ወደ ቤታቸዉ አልገባም፡፡ እንዲሁ ከፋሲካችን ከክርስቶስ ሥጋና ደም በልተዉ በደመ ማኅተሙ የታተሙትን ሁሉ ሞት አያገኛቸዉም፡፡ እነርሱ የበራቸዉን ጉበንና መቃን በሚታይ ቦታ ላይ እንደቀቡት በእኛም በግንባራችን ላይ እርሱ ያስቀባዉና  የሚያነብበዉ ማኅተም አለ፡፡ነቢዩ ሕዝቅኤል ‹‹ እግዚአብሔርም፦ በከተማይቱ በኢየሩሳሌም መካከል እለፍ፥ በመካከልዋም ስለ ተሠራው ርኵሰት ሁሉ በሚያለቅሱና በሚተክዙ ሰዎች ግምባር ላይ ምልክት ጻፍ አለው። እኔም እየሰማሁ ለሌሎቹ እርሱን ተከትላችሁ በከተማይቱ መካከል እለፉ ግደሉም ዓይናችሁ አይራራ አትዘኑም፤ ሽማግሌውንና ጐበዙን ቈንጆይቱንም ሕፃናቶቹንና ሴቶቹን ፈጽማችሁ ግደሉ ነገር ግን ምልክቱ ወዳለበት ሰው ሁሉ አትቅረቡ፤ በመቅደሴም ጀምሩ አላቸው። በቤቱም አንጻር ባሉ ሽማግሌዎች ጀመሩ ›› /ሕዝ 94-6/ ሲል እንደገለጸልን ምልክቱን እርሱ ያስቀረጸባቸዉ ብቻ ከዘላለም ሞት ይድናሉ።

በነቢዩ እንደተገለጸዉ ግን ፍርድ ከቤቱ መቅሰፍቱም በቤቱ ከተገኙ ሽማግሌዎች የጀመረዉ በቤቱ ከምንኖረውም ውስጥ ከሞት የማናመልጥ እንዳለን ያመለክታል፡፡ ይህ ደግሞ የሚከሰተዉ የፋሲካዉን በግ ባለመብላት ብቻ ሳይሆን ከላይ የተጠቀሱትን ሕጎቹን አክብሮ ባለ መብላት ምክንያት ነዉ፡፡ስለዚህ እንዲህ ያለዉ ነገር እንዳይገጥመን አስቀድመን ሕጎቹን አንድ በአንድ እንመልከታቸዉ፡፡
1.    ባዕድ አይብላዉ
ከላይ በሰፊዉ እንደተዘረዘረው ሦስት አካላት እንዳይበሉት ታዝዟል፡፡ መጻተኛና እንግዳ( ከእሥራኤል ወገን ያልሆነ) እንዲሁም በዘመኑ የነበሩ ባሮች ካልተገዘሩ ( አሁንም ባዕዳን የሆኑ) አይብሉ ተብሏል፡፡ ምክንያቱም የመንጻቱንም ሆነ ሌላዉን የቅድስና ሕግ አያውቁትም፡፡ ይህን ሳያውቁ ቢበሉት ደግሞ ‹‹ትእዛዝን የሚያቃልል በትእዛዝ ተይዞ ይጠፋል›› /ምሳ 1313/ ተብሎ እንደተጻፈ ጥፋትና መቅሰፍትን እንጂ ሥርየትና ሕይወትን አያገኙም፡፡ ይህም ልክ እንደ ይሁዳ ማለት ነዉ፡፡ ይሁዳ ራሱን ከአይሁድ የተንኮል ምክር አስተባብሮ ልቡናዉንና መንፈሱን ከሐዋርያት ኅብረት ሲያወጣ ባዕድ ሆነ፡፡ በዚሁ የባዕድ ልቡናዉ ሆኖ ከሥጋዉና ከደሙ ቢቀበልም ሳይጠቅመዉ ቀረ፡፡ በደኅንነት መሥዋዕቱም ጊዜ በግና ፍየል ለመሥዋዕት የሚቀርብበት ምክንያት ይህንኑ በምሳሌ ለማስረዳት ነበር፡፡ ምክንያቱም ጌታ የመሥዋዕት በግ ቢሆንም ተቀባዮቹ ወይም ቆራቢዎች ግን እንደ ይሁዳና ሐዋርያት የተገባቸዉና ያልተገባቸዉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የጌታ ሥጋና ደም ለተገባቸዉ (ሐዋርያትን ለመሰሉት) የበግ መሥዋዕት ሲሆንላቸዉ ላልተገባቸዉ (ይሁዳን ለመሰሉት) ደግሞ የፍየል ይሆንባቸዋል ማለት ነዉ፡፡ ይህም ማለት ግን ጌታ በፍየል መሥዋዕቱ ተመስሏል ማለት አይደለም፤ አይመሰልምም፡፡ ነገር ግን በኦሪቱ ፍየል ለደኅንነት መሥዋዕት የሚቀርበዉ ላልተገባቸዉ ሰዎች የጌታ ሥጋና ደም እንሚለወጥባቸዉ ወይም እንደማይጠቀሙበት ለማጠየቅ (ለማስረዳት) ነዉ፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴዉ ‹‹ እሳት ማሕየዊ ለርቱዓነ ልብ ለእለ ይገብሩ ፈቃዶ፤ እሳት በላዒ ለዓማጽያን ለእለ ይክህዱ ስሞ ትእዛዙን ለሚፈጽሙ ቅኖች የሚያድን የሕይወት እሳት ነዉ፤ ስሙን ለሚክዱ ለዓማጽያን ደግሞ የሚያቃጥል የሚያፍገመግም እሳት ነዉ›› እንዳለ እንደሚበሉት ሰዎች ሕይወት ይለወጥላቸዋል ወይም ይለወጥባቸዋል፡፡ አሁን ‹‹ስሙን ለሚክዱ›› ሲል እግዚአብሔርን የማያምኑ ሰወች ሊቆርቡ ይመጣሉ ብሎ ሳይሆን ስሙን እየጠሩ እንደ ይሁዳ ልቡናቸዉ በፍቅረ ንዋይና በተንኮል ከተያዘ የማያምኑና አማጽያን የሚባሉትእነርሱ መሆናቸዉን ለማስረዳት ነዉ፡፡ ስለዚህ ባዕዳን አይብሉት የተባለዉ ሕጉን የማያከብሩ፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር የማይኖሩ አይብሉት ለማለት ነዉ፡፡ ሊበሉት ከፈለጉ ግን ‹‹ወንዶቹ ይገረዙ፤ እንደ አገር ልጅም ይሆናሉ›› የተባለዉ ለዚህ ነዉ፡፡ ምክንያቱም ችግሩ ምድራዊ ዘራቸዉ ሳይሆን አለማመናቸዉ ነበርና፡፡ ስለዚህ አሁንም ፋሲካችንን ስናከብር እንደ ይሁዳ አካላችንን ቤተ ክርስቲያን ዉስጥ ሆኖ ሐሳባችንና ዓላማችን ግን ቤተ ክርስቲያንን መጠቀሚያ ሊያደረጓት ከሚሹ ከጠንቋዮች፣ ከክፉ ፖለቲከኞች፣ ሊለዉጧት ከተነሡ መናፍቃንና ተሐድሶዎች ወይም ይህን ከመሰለና ለቤተ ክርስቲያን ባዕድ ከሆነ ማንኛዉም ሐሳብ ጋር ያለን ከሆነ የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ያሉ ሰዎች ፋሲካውን ሊቀበሉ አይገባቸዉም ይለናል፡፡ሊቁ አባ ሕርያቆስ ‹‹ በአማን ቁርባን ውእቱ ዘኢይክሉ ይጥዐሙ እምኔሁ ግሙናነ መንፈስ፤ መንፈሳቸዉን ያረከሱ ሰዎች ከእርሱ ሊቀበሉት የማይቻላቸዉ በእዉነት ቁርባን ነዉ›› /. 5/ እንዳለዉ ባዕዳን የተባሉት እነዚህ በአገልግሎትም ሆነዉ ነገር ግን በሐሳብና በውስጣቸዉ መንፈሳቸውን ያረከሱ ሰዎች ናቸዉ፡፡ መብላት ከፈለጉ ይገረዙ የተባለዉም የሥጋ ሸለፈትን ማስወገድ ምሳሌነቱ የኃጢኣት ሸለፈትን ማለትም መንፈሳቸዉን ያረከሰዉን ነገር በንስሐ ቆርጠዉ ጥለዉ ይምጡ ማለት ነዉ፡፡ በዚህ ጊዜ ይቻላል፤ ቢቀበሉትም ሕይወት ይሆናል፡፡ በኦሪቱ ‹‹ እንደ አገር ልጅም ይሆናል›› ማለትም ለሰማያዊት ሀገር ለገነት ለመንግሥተ ሰማያትም የተገባ ይሆናል ማለት ነዉና ጽድቁን ገንዘብ ያደርጋል፡፡   
2.     በአንድ ቤትም ይበላ
ሌላዉ ስለፋሲካዉ የተሰጠዉ ትእዛዝ በአንድ ቤት የመበላቱ ጉዳይ ነዉ፡፡ በዚያ ጊዜ በግብጽ እያሉ እንኳ ከአንዱ ቤት ወጥቶ እንዲሔድ አልተፈቀደም፡፡ ይህም ከላይ እንደገለጽነዉ ሥጋዉና ደሙ በአንድ ቤት በቤተ ክርስቲያን ብቻ ልንቀበለዉ እንደሚገባ የተሠጠ ትዕዛዝ በመሆኑ ነዉ፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር በቅዱስ ቦታው ለድሀ አደጎች አባት፥ ለባልቴቶችም ዳኛ ነው። እግዚአብሔር ብቸኞችን በቤት ያሳድራቸዋል፥ እስረኞችንም በኃይሉ ያወጣቸዋል፤ ዓመፀኞች ግን በምድረ በዳ ይኖራሉ።›› / መዝ 68 5-6/ ሲል እንደገለጸው ምድረበዳዉ የሌሎች ነዉ፡፡ እኛ እንደተጻፈው እግዚአብሔር በቤቱ እንዲያሳድረን የእርሱንም ሥጋና ደም (የፋሲካዉን በግ) እንዲመግበን አስቀድሞ ነግሮናልና ሌላ ቦታ እንበላዉ ዘንድ ክብሩንም ከአማናዊነት ወደ ምሳሌነት እናወርደዉ ዘንድ አንገዳደረዉም፡፡ ይህ ፋሲካ የሚበላባት ቤቱም ቤተ ክርስቲያን አንዲት ብቻ ናት፡፡ የተረፈው ሥጋ እንኳ ከቤት ወጥቶ ወደ ምድረ በዳ አይጣል የተባለዉ የክርስቶስ ሥጋና ደም ከቤተ ክርስቲያን ዉጭ ሌላ ቦታ ሊጣልም ሊበላም ስለማይገባ ነዉ፡፡ አባ ጄርም ይህን በተረጎመበት ድርሳኑ የኖኅ መርከብ ዉስጥ የገቡት ብቻ ከጥፋት ዉኃ እንደዳኑ ፤ዳግመኛም በረዓብ ቤት የነበሩ ብቻ ከኢያሪኮ ጥፋት እንዳመለጡ በአንዲት ቤተ ክርስቲን ተሰባስበዉ ሥጋዉንና ደሙን የበሉ ብቻ ይድናሉ ይላል፡፡
3.     አጥንቱ መሰበር የለበትም
ስለ መሥዋዕቱ ከተሰጠዉ ትእዛዝ አንዱ አጥንቱ አይሰበር የሚለዉ ነዉ፡፡ ይህም ስለ እኛ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበዉ በግ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በግርፋቱና እየተገፋ በወደቀ ጊዜ፣በችንካሩም ሆነ ለንጊኖስ በጦር በወጋዉ ጊዜ ከአጥንቱ አንድም እንኳ አንደማይሰበር አስቀድሞ የተነገረ ምሳሌያዊ ትንቢት ነዉ፡፡ ይህንንም ወንጌላዊ ዮሐንስ ‹‹ ጭፍሮችም መጥተው የፊተኛውን ጭን ከእርሱም ጋር የተሰቀለውን የሌላውን ጭን ሰበሩ፤ ወደ ኢየሱስ በመጡ ጊዜ ግን እርሱ ፈጽሞ እንደ ሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፤ ነገር ግን ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው፤ ወዲያውም ደምና ውኃ ወጣ።ይህ የሆነ። ከእርሱ አጥንት አይሰበርም የሚል የመጽሐፉ ቃል እንዲፈጸም ነዉ›› /ዮሐ 19 32-36/ በማለት አረጋግጦልናል፡፡
በግብጽ የነበሩት ሕዝቡም ሙሴ እንደነገራቸዉ አድርገው ለእግዚአብሔር እንደታዘዙ ሁሉ እኛም እንዲሁ ለእግዚአብሔር በሐዋርያትና በተከታዮቻቸዉ እንደ ሰማነዉ አድርገን ለእግዚአብሔር መታዘዝ ይገባናል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም የምትፈጽመው ሥርዓተ አምልኮ በሙሉ እንዲህ የታዘዘውንና የተተረጎመውን (ጌታ አማነዊ ያደረገውን) ብቻ ነዉ፡፡ በርእሳችን እንደተቀመጠዉ መፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞን ከተለዩት በተለየዉ ቅኔያዊ መዝሙሩ በመኀልየ መኀልይ ላይ ግራዉ ከራሴ በታች ናት የሚለን ይህችን ኦሪት ነዉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን መጻሕፍተ ኦሪትን ዕቃ ቤት እንደተቀመጠ መታሰቢያ ብቻ ሳይሆን ተርጉማ አማነዊ በሆነ መንገድ የምትፈጽማት ስለሆነ ከራሴ በታች ናት አለቻት፡፡ እንዲህ የምትለዉ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ራሷ ደግሞ ክርስቶስ ነዉ፡፡ ስለዚህ ኦሪትን ‹‹ከራሴ በታች›› ስትል ሥጋዌን አስቀድማ በምሳሌ ያሳየች የትንሣኤ በዓላችንን በፋሲካ በዓሏ፣ ለመሥዋዕተ ሐዲስ ለክርስቶስ ሥጋና ደምም ምሳሌዉን ስታሳይ የቆየች ቀድማ የተላከች መመሪያና በዚያም መሠረት እንድንፈጽም እንደ ካርታ ሆና ያገለገለች ስለሆነ ከራሴ በታች ጉዝጓዜ ትራሴ ትላታለች፡፡ በሰሙነ ሕማማቱም ስትነበብ የምትሰነብተዉ ለዚህ ነዉ፡፡ መሠረትና መደላድልነቷን ትራስነቷን ልንረሳዉ አንችልምና፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ቤተ ክርስቲያን የሚያሰኛትም ይህ ሐዲስ ኪዳንን በብሉይ ኪዳን ላይ ብሉይን ከሥር ሐዲስን በላዩ ማነጽ መቻሏ ነዉ፡፡ሐዋርያዉ ቅዱስ ጳዉሎስም ‹‹በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤›› /ኤፌ 2 20/ ሲል እንደገለጸዉ መሠረታችን የነቢያትም የሐዋርያትም ነዉ፡፡ ኦሪትና ነቢያትን ፈጽሞና ተርጉሞ ከሐዲስ ኪዳን ጋር ያገናኘ የማዕዘኑ ራስም እንደተባለዉ ጌታችን ነዉ፡፡ራሱ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሉቃስና ቀልዮጳ በእርሱ ትንሣኤ አላምን ብለው ከኢየሩሳሌም ወጥተዉ ወደ ኤማሁስ ሲጓዙ መንገደኛ መስሎ እየተከተለ ኦሪትንና ነቢያትን ተርጎሞላቸዋል፡፡ ወንጌላዊዉ ቅዱስ ሉቃስ ‹‹ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ ስለ እርሱ በመጻሕፍት ሁሉ የተጻፈውን ተረጐመላቸው›› /ሉቃ 2427/ ሲል እንደገለጸው በርግጥም  ክርስቶስ ለቤተ ክርስቲያን ግራው ኦሪትን አንተርሷታል፡፡ ቀኙ ወንጌልም አቅፋታለች፡፡ እውነተኛይቱና አንዲቱ ቤተ ክርስቲያን በዚህ ተጠብቃ ጸንታ ትኖራለች፤ የሰሎሞን ልዩ የዝማሬ ቃልም የሚያስረዳዉ ቤተ ክርስቲያንን ግራው የተባለች አሪትን አንተርሶ ቀኙ በተባለች ወንጌል አቅፎ (በዕቅፉ ዉስጥ አድርጎ) ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቃት ክርስቶስ ነዉ ሲለን ነዉ፡፡ ስለዚህም በነፍስ የዕውቀት ገንዘብ የበለጸጉ ሁሉ የቤተ ክርስቲያን አካልነታቸዉን አውቀዉ በእንደዚህ ያለዉ በዓል ግራህ ከራሴ በታችእያሉ አሪት የወንጌሉን ባለቤት ሙሽራውን ክርስቶስን ያመሰግኑታል፡፡ እነርሱም ራሳቸዉም የሚኖሩት በክርስቶስ የማዳን ዕቅፍ ዉስጥ ነውና፡፡ ነፍስ ኅርይት ሁሉ ለራሷም ግራ ሥጋዊነትን ከራሴ (ከሃሳቤ) በታች ጥለህልኛልና ቀኝ መንፋሳዊነትንም በትንሣኤህ አጎናጽፈኸኛልና እያለች ታመሰግነዋለች፡፡ መፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞን ስለ ጥበብም ተገብቶ ግራ ሓሳርና ውርደት( በግራ መቆም) እና ቀኝ የተባለ ክብር ሽልማትም (ቁመተ የማን) ከአንተ ዘንድ ነዉና እያለም ያመሰግናል፡፡ስለዚህም በዓላችን ግራው ፋሲካን ተንተርሣ በቀኝ ትንሣኤ ክርስቶስ ታቅፋ የምትከበር የእውነተኛ ፍቅር በዓላችን ናት ማለት ነዉ፡፡
ክርስቲያኖች ሆይ በዓላችንን በዓለ ፋሲካም በዓለ ትንሣኤም የምንለዉ በእነዚህ በኦሪቱና በሐዲሱ፣ በምሳሌዉና በአማናዊዉ፣ በንባቡና በትረጓሜዉ በአጠቃላይ  በሁለቱም እጆች በግራና በቀኝ የታቀፈችና የተያዘች ስለሆነ ነዉ፡፡ በአይሁድ ፋሲካ የክርስቶስን ማዳን እንደተነገረንና በዚያ በብሉይ የነበሩት አበዉ ሁሉ ሲጠባበቁት እንደኖሩት በክርስቶስ ትንሣኤም ትንሣኤ ሙታንና (የክብርና የውርደት) ዘለለማዊ ሕይወት እንዳለ ተነግሮናል፡፡ ስለዚህም ለራሳችን የክብር ትንሣኤም እየተዘጋጀን በቀኝ ለመቆም እንዲያበቃን እየተማጸንን በደስታና በመንፈሳዊ ሐሴት እናከብረዉ ዘንድ የእርሱ ቸርነት የድንግል እናቱ አማላጂነት አይለየን፤ አሜን፡፡



7 comments:

  1. kala heiwate yasamachohe

    ReplyDelete
  2. ቃለ ህይወት ያሰማልን።

    ReplyDelete
  3. kale hiwot yasemalin. Endezih aynet sewoch le EOTC yasfelgatal

    ReplyDelete
  4. Dn.Birhanu Egziabher yasfetsmih KHY.

    ReplyDelete
  5. It was so great reading this. Yemininoribet yadergilin zend fekadu yihun. GOD bless you Mele!!! Kale Hiwot Yasemalin!!!

    ReplyDelete
  6. Kale Hiywot Yasemalin

    ReplyDelete