Monday, April 30, 2012

ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ


ሰማዕት ማለት ምስክር ማለት ሲሆን በሃይማኖት ምክንያት የተገደለ፣ መከራ የደረሰበት ሰማዕት ይባላል። (ሐዋ.22፡20) የመጀመሪያዎቹ የሐዲስ ኪዳን ሰማዕታት ሐዋርያትና አርድዕት ናቸው።
ቅዱሳን ሰማዕታት የሚባሉት “እግዚአብሔርን ካዱ ለጣዖት ስገዱ” ሲባሉ “እግዚአብሔርን አንክድም ለጣዖት አንሰግድም” በማለት በዓላውያን ነገሥታት ፊት ቀርበው ሳያፍሩና ሳይፈሩ ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክነት የመሰከሩ ናቸው። በዚህም ምክንያት ተዘርዝሮ የማያልቅ የመከራ ዓይነት ተቀብለው ለፈጣሪያቸው ክብር ሲሉ ደማቸውን ያፈሰሱ፣ አጥንታቸውን የከሰከሱ፣ ሕይወታቸውን ያጡ ናቸው።
በእሳት ተቃጥለዋል፣ በውኃ ተቀቅለዋል፣ በሰይፍ ተመትረዋል፣ በመጋዝ ተተርትረዋል፣ በመንኩራኩር ተፈጭተዋል (መንኩራኩር የሚባለው በዘመነ ሰማዕታት የነበረ ዘመናዊ የወፍጮ መሳሪያ ነው።)፣ እንደከብት ቆዳቸው ተገፏል፣ ወደጥልቅ ባህር ተጥለዋል። በዚህ ሁሉ መከራ ውስጥ ከሃይማኖታቸው አላፈገፈጉም፤ እንዲያውም ሌሎች “እኔ በእነርሱ አምላክ አመልካለሁ” እንዲሉ አድርገዋቸዋል።

Saturday, April 21, 2012

ዳግም ትንሣኤ



ጌታችን በተነሣበት ዕለት የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ተሰብስበው ሳለ ጌታችን በመካከላቸው ቆመና "ሰላም ለእናንተ ይሁን "አላቸው፡፡ የነበሩበት ቤት በሩም መስኮቱም ተቆልፎ ስለነበር ደቀ መዛሙርቱም በጣም ደነገጡ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም  "አትፍሩ እኔ አምላካችሁ ነኝ" ብሎ የተወጋ ጎኑን እና የተቸነከሩ እጆቹን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ጌታ ከሞት መነሣቱን አመኑ፡፡ ደቀመዛሙርቱንም(ተማሪዎቹንም) ሕዝቡን እንዲያስተምሩ ላካቸው፡፡

Thursday, April 19, 2012

ፋሲካ - የፋሲካ በግ - ትንሣኤ



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን፡፡
 በዲ/ ብርሃኑ አድማስ
እሥራኤልን ከግብጽ እየመራ የወጣው ሙሴ ሕዝቡን ከግብጽ ይዞ መውጣት ይቻለው ዘንድ የታዘዘው ታላቁ ትእዛዝ ፋሲካን በግብጽ ማክበር ነበር፡፡ ፋሲካ የሚባል በዓል ከዚያ በፊት ኖሮም ተከብሮም አያውቅም ነበርና በዝርዝር ማድረግ የሚገባቸዉ ሁሉ ተነገራቸዉ፡፡ ቀኑ በእነርሱ አቆጣጠር በአቢብ ወር በዐሥራ አራተኛዉ ቀን ይከበራል፡፡ ነውር የሌለበት የአንድ ዓመት ጠቦት በግ  ይመርጣሉ፡፡ በምድረ በዳ ሲመሽ ያርዱታል፡፡ ደሙን ወስደዉ የቤታቸዉን በር ሁለት መቃኖችና ጉበኑን ይረጩታል፡፡ ሥጋውን በሌሊት በእሳት ጠብሰው ይበሉለታል፡፡ ጥሬውንና በውኃ የተቀቀለዉን አይበሉም፡፡ የተረፈውን ሌሊቱን በእሳት ያቃጥሉታል፡፡በፍጥነት ይበሉታል፡፡ ከዚያ በኋላ ለሰባት ቀን የቂጣ በዓሉን ያደርጋሉ፡፡ ቂጣዉም ምንም እርሾ ያልገባበት ይሆናል፤ …./ዘፍ 12 1-36/፡፡

Thursday, April 12, 2012

ጸሎተ ሐሙስ



ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው።

እራትም ሲበሉ ዲያብሎስ በስምዖን ልጅ በአስቆሮቱ በይሁዳ ልብ አሳልፎ እንዲሰጠው አሳብ ካገባ በኋላ፥

ኢየሱስ አብ ሁሉን በልጁ እንደ ሰጠው ከእግዚአብሔርም እንደ ወጣ ወደ እግዚአብሔርም እንዲሄድ አውቆ፥

ስምዖን ጴጥሮስ
ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤

በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ።

ወደ ስምዖን ጴጥሮስም መጣ፤ እርሱም፦ ጌታ ሆይ፥ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን? አለው።

ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፥ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ አለው።

ጴጥሮስም፦ የእኔን እግር ለዘላለም አታጥብም አለው። ኢየሱስም፦ ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም ብሎ መለሰለት።

ስምዖን ጴጥሮስም፦ ጌታ ሆይ፥ እጄንና ራሴን ደግሞ እንጂ እግሬን ብቻ አይደለም አለው።

ኢየሱስም፦ የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፥ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፤ እናንተም ንጹሐን ናችሁ፥ ነገር ግን ሁላችሁ አይደላችሁም አለው።

Wednesday, April 11, 2012

ዘረቡዕ (ረቡዕ) - ሰሙነ ሕማማት




             በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አዘጋገብ መሠረት ሦስት ነገሮች በዕለተ ረቡዕ ተደርገዋል፤ እነርሱም የሚከተሉት ናቸው፡፡

1. የካህናት አለቆች÷ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ ተማክረዋል፤

2. ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡

3. ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ 30 ብር ተመዝኖለታል፡፡

            የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምንት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐሲኒሃ ድርየምይባላል፡፡ በዚህ ሸንጐ ላይ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲሆኑ የተቀሩቱ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ 72 አባላት የነበሩት ሲሆን የሚመራው በሊቀ ካህናቱ ቀያፋ ነበር፡፡

Tuesday, April 10, 2012

ማክሰኞ (ዘሰሉስ) - ሰሙነ ሕማማት


                 በዚህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ናቸው፡፡ ጥያቄውምበማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?” የሚል ነበር፡፡ የካህናት አለቆች ያቀረቡት ጥያቄ ነበር፡፡ ጌታችን ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማድረጉን ተያይዞ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ሰኞ ከቅጠል ብቻ በቀር ፍሬ ያላገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፤ በማስከተል ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡ ማቴ.21÷23-25 ማር.11÷27 ሉቃ.20÷1-8፡፡ ከላይ እንደ ተገለጸው ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩት ተአምራትና የኃይል ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀናቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡

            
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ በአንድ አገር የንግድ ቦታን የሚያጸድቅ መንግሥት መሆኑ እሙን ነው፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡት ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ አልመለሰም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሷል፡፡በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ፤ በማን ሥልጣን ነው ይህን የምታደርገው?” ነበር ያሉት፡፡ በራሴ ሥልጣን ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡
  

Monday, April 9, 2012

ሰኞ (ሰኑይ) -ሰሙነ ሕማማት


              ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሳዕና ማግሥት ጌታችን ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሁለት ነገሮችን አድርጓል፡፡
አንደኛ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡
ሁለተኛ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል፡፡ /ማቴ.21÷12-17 ማር.11÷17 ሉቃ.19÷45-46፡፡/ በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥበማግሥቱ ተራበየሚል ቃል እንመለከታለን፡፡

              ነቢዩ ኢሳይያስእግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም” /ኢሳ.46÷25/ ይላል፡፡ በቅዱስ ወንጌልምበመጀመሪያ ቃል ነበርይላል፡፡ ቃል ቀዳማዊ እንደ ሆነ፣ ቃል በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፣ ያም ቃል እግዚአብሔር ነው ተብሎ ተጽፏል፡፡ ዮሐ.1÷1-2፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱም ሲያስተምርየእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፡ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው” /ዮሐ.4÷34/ ሲል ተናግሯል፡፡ ነቢዩ እግዚአብሔር እንደማይራብ ተናግሯል፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

Sunday, April 8, 2012

ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት .....(ክፍል ሁለት)



 ጸሎተሐሙስ

 በብሉይ ኪዳን የቂጣ በዓል የሚለውን ትርጉም ከመስጠቱ በተጨማሪ ጌታችን ምስጢረ ቁርባንን ከምስጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ስልሆነ ታላቅ የምስጢር ቀን ነው። በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱ እንደተለመደው ይከናወናሉ ለየት ያለው ሥርዓት መንበሩ /ታቦት/ ጥቁር ልብስ ይለብሳል ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል ቤተክርስቲያኑ በማዕጠንት ይታጠናል።

በዘጠኝ ሰዓት

              ዲያቆኑ ሁለት ኮስኮቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ ጸሎተ አኮቴት የተባለ የጸሎት ዐይነት ተጸልዮ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ /በሊቀ ጳጳሱ/እጅ ተባርኮ የሕጽበተ እግር ሥርዓት ከካህናት እስከ ምእመናን ከወንዶች እስከ ሴቶች በካህኑ እስተናጋጅነት ይከናወናል።