Tuesday, January 31, 2012

ቅዱስ ቶማስ እና የሰማዩ ቤተ መንግሥት


ሐዋርያው  ቅዱስ  ቶማስ
በህንድ ሀገር ታከሻሊላ በተባለ ከተማ ጎንዶፓረስ የተባለ ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ንጉሥ በኢየሩሳሌም ስለ ነበረው የንጉሥ ሰሎሞን ቤተ መንግሥት ዝና እየሰማ እርሱም በሀገሩ ማሠራት ይፈልግ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ነጋዴዎች በየሀገሩ ሲጓዙ የታወቀ ግንበኛ  እንዲያመጡለት አዘዛቸው፡፡

ይህንን መልእክት ከሰሙት ነጋዴዎች መካከል አንዱ ፋርስ ወደሚባለው ሀገር ተጓዘ ከዚያም ያ ነጋዴ አንዱ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስን አገኘው፡፡ ነጋዴው ቶማስ ከኢየሩሳሌም እንደመጣ ሲሰማ የግንበኝነት ሙያ ይችል እንደሆነ ጠየቀው፤ ሐዋርያው ቶማስ ወደ ህንድ ሄዶ ማስተማር ይፈልግ ነበር፡፡ ስለዚህም ይህንን ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም ለመሔድ “በኢየሩሳሌም ሳለሁ ህንፃ በመገንባት እኖር ነበር፡፡” አለው፡፡


ነጋዴውም በጣም ተደስቶ ቶማስን ወደ ህንድ ወሰደው፡፡ ንጉሡም የቶማስን ሙያ ሲሰማ በጣም ደስ አለው፡፡ ከዚያም ከከተማው አጠገብ ወደሚገኘው ሔዶ ቶማስን ወሰደውና በጫካ የተሞላውን ሜዳ እያሳየ ቤተ መንግሥቱ በዚያ ቦታ ላይ እንዲሠራ ነገረው፡፡ ቅዱስ ቶማስ የቤተ መንግሥቱን አሠራር ሲነግረው ንጉሡ ተሠርቶ እስከሚያየው ቸኮለ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ንጉሡ ለህንጻው መሥሪያ ብዙ ገንዘብ ለቅዱስ ቶማስ ይልክለት ጀመር፡፡

ቅዱስ ቶማስ ግን ገንዘቡን ሲያገኝ የሚሔደው ወደ ድሆች መንደር ነበር፡፡ በዚያም ለተራቡት ምግብ፣ ልብስ ለሌላቸው ልብስ፣ መጠለያ ቤት ለሌላቸው ደግሞ ቤት እየገዛ መስጠት ጀመረ፡፡ የታመሙትን እያዳነና እየስተማረ ይኖር ጀመረ፡፡

ንጉሥ ጎንዶፓረስ ለሕንፃው መሥሪያ የመደበው ገንዘብ እና ጊዜ እንዳለቀ፣ ቤተ መንግሥቱን ሊጎበኝ መጣ፡፡ ወደ ቦታው ደርሶ ቢመለከት እንኳን ሕንፃው ሊሠራ ጫካው አልተነካም፡፡ ንጉሡም በዚያ የሚያልፍ መንገደኛ ጠርቶ ቶማስ የታለ? ሲል ጠየቀው፡፡

“ቶማስ በድሆች መንደር የተቸገሩትን እየረዳና እያስተማረ ይገኛል፡፡” ሲል መንገደኛው መለሰለት፡፡ “እርሱስ ጥሩ ግን የሰራልኝ ቤተ መንግሥት የታለ?” ብሎ መንገደኛውን ጠየቀው፡፡ መንገደኛውም “በድንጋይ የተሠራ ቤተ መንግሥት ላያዩ ይችላሉ፤ ጌታዬ፤ ነገር ግን ሕዝብዎ በጣም እንደተደሰተ መመልከት ይችላሉ፡፡” አለው፡፡

በዚህ ጊዜ ንጉሡ ያ ሁሉ ገንዘብ እንደባከነበት መጠራጠር ጀመረ ወዲያው ወታደሮቹ ቶማስን ፈልገው እንዲያመጡ ላካቸው፡፡ ቅዱስ ቶማስ ተይዞ እንደመጣ “ቤተ መንግሥቴን ለምን አልሠራህልኝም ጫካው እንኳን መቼ ተነሣ?” ብሎ ጠየቀው፡፡ ቶማስም “በእርግጥ በምድር ላይ የድንጋይ ቤተ መንግሥት ላያዩ ይችላሉ፡፡ እኔ ግን በሰማይ ላይ ቤተ መንግሥት ሠርቼሎታለሁ፡፡” አለው፡፡

ያን ጊዜ ንጉሡ ተቆጣ፤ ቶማስን እጅ እግሩን እንዲያሰቃዩት አዞ እስር ቤት አስገባው፡፡ በዚያች ሌሊት የንጉሡ ወንድም ልዑል ጋድ በድንገት ታሞ ሞተ፡፡ የጋድ ነፍስ በመላእክት ታጅባ ወደ ሰማያት ወጣች፡፡ የጋድን ነፍስ ካጀቧት መላእክት አንዱ ብዙ ቤተ መንግሥታትን እያሳያት “እንድትኖሪበት ደስ ያለሽን ምረጪ፡፡” አላት፡፡ የጋድ ነፍስም ከቤተ መንግሥታቱ ሁሉ የሚያምረውን መረጠች “ይህ ቤተ መንግሥት የአንቺ አይደለም፤ ቶማስ ለንጉሥ ጎንዶፓረስ የሠራለት ሰማያዊ ቤተ መንግሥት ነው፡፡”

ጋድ ሊቀብሩት በተሰበሰቡት ሰዎች መካከል ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ተነሣ፡፡ ከዚያም ያየውን ሁሉ ለንጉሡ እና ለተሰበሰቡት ሰዎች ነገራቸው፡፡

ንጉሡ ይህን ሲሰማ በቶማስ ላይ በሠራው ሁሉ አዘነ፣ ያሰበው ቤተ መንግሥት መሠራቱን ሲሰማ ቶማስን ከእስር ቤት አስመጣው፡፡ እራሱ እና ቤተሰቡም በክርስቶስ አምላክነት አምነው ተጠመቁ፡፡ ለቶማስም ያለውን ገንዘብ ሁሉ “ሌላም ቤተ መንግሥት ሥራልኝ” እያለ ይሰጠው ጀመር፡፡ የሀገሩ ሰዎችም እንደርሱ ያደርጉ ጀመር፡፡

የተቸገሩትን መርዳት እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ መልካም ሥራ ነው፡፡ የተቸገሩ ሰዎችን የምንረዳ ከሆነ ደግሞ በምድር ላይ አይተነው የማናውቀውን እጅግ በጣም ያማረ ቤት ያሰጠናል፡፡


በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያንም ምጽዋት ሁለት ታላላቅ የመስጠትና የመቀበል ጥቅሞችን የያዘ ነዉ፡፡ የመጀመሪያዉ ሰብአዊ ጠቀሜታ ነዉ፡፡ በየትኛዉም ማኅበረሰብ ዉስጥ በተለያየ ምክንያት መሥራት የማይችሉ ሰዎች ይኖራሉ፤ አሉም፡፡ ባይሠሩም ምግብ ግን ያስፈልጋቸዋል፡፡ ሌላዉም አይመገቡ ሊል አይገባዉም፡፡ በርግጥ ኮሚኒስቶች ሥራን እናስከብራለን ብለዉ‹‹የማይሠራ አይብላ›› ይሉ ነበር ይባላል፡፡ ይህ ግን ሥራን አያስከብረዉም፡፡ ምክንያቱም ሰዉ መሥራት እየፈለገም በሕመም፣ በዕድሜና(አረጋዊያንና ሕፃናት) በተለያዩ ምክንያቶች ላይሠራ ስለሚችል ‹‹የማይሠራ አያብላ›› የሚለዉ የኮሚኒስቶች መፈክር ሊተገበር የሚችል አይደለም፡፡ እንደኔ ግምት ሀሳቡን ከመጽሐፍ ቅዱስ ነበር የወሰዱት፤ ነገር ግን በትክክል ካለ መኮረጂ ወይም እናሻሽል ከማለት የተበላሸባቸዉ ይመስለኛል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚለዉ ‹‹ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› /2 ተሰ 310/ነዉ፡፡ ምክንያቱም አሁን በእኛ ሀገር እንደሚታየዉ ሥራ ያለዉ (የተቀጠረ፣ ሰዓት ቆጥሮ የሚፈርም፣ ለመብላት ሲል መሥሪያ ቤት የሚዉል) ነገር ግን መሥራት የማይፈልግ ሺህ ሰነፍ አለ፡፡ መጽሐፋችን አይብላ ብሎ የሚከለክለዉ እንዲህ ያለዉን አስቸጋሪ ሰነፍ ነዉ፡፡ጠቡም ከስንፍና ጋር እንጂ ከሰዉ ጋር አይደለም፡፡ስለዚህ ከላይ በተገለጹትም ሆነ በሌሎች ምክንያቶች መሥራት ለማይቻላቸዉ ሰዎች መመጽዎት ከማንኛዉም ሰብአዊ ፍጡር የሚጠበቅ ተግባር ነዉ፡፡ በዚህም ሰዉ ለወገናቸዉ ሁሉ ጠንክረዉ ከሚረዱ ከእንስሳትና ከአራዊት እንኳ የማያንስ ፍጥረት ይሆናል እንጂ ልዩ ፍጡር ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ሰብአዊነት በየትኛዉም ሀገር ሰዎችን መኖር የሚያስችል ገንዘብ በመስጠት የሚፈጸም አለም አቀፋዊ ሰብአዊ መብት ሆኖአል፡፡
       
         በየትኛዉም ሀገርም የሚመጸወቱት ሰዎች አሉ፡፡ምጽዋቱ የሚሰበሰበዉም ከሚሠራዉ ሕዝብ ቢሆንም የሚሰበሰብበት ሥርዓት ግን ግብር(tax) ይባላል፡፡ ይህን በማድረጋችንና ወገናችን ከችግርና ከረሀብ ተላቅቆ በማደሩም እርካታንና ሰላምን እናገኛለን፤ ለእኛም የኑሮ ዋስትና ይሆነናል፡፡ በዚህ መሠረታዊ ምክንያት አንድ ኦርቶዶክሳዊ ለአንድ የተቸገረ ሰዉ ሃይማኖቱን ወይም ምግባረ ብልሹነቱን ሳያይ መመጽወት ይኖርበታል፤ የሚመጸዉተዉ ለሰዎቹ እንጂ ለሃይማኖታቸዉ ወይም ለምግባራቸዉ አይደለምና፡፡በሌላ በኩል ቢያንስ የመኖር መብትን የማያስቀር የሀብት መከፋፈያ መንገድ ነዉ ማለት ነዉ፡፡

             ሁለተኛዉና መሠረታዊ ጥቅሙ ደግሞ በሰማይ የምንቀበለዉ ጽድቅ ነዉ፡፡ በርግጥ ጽድቁ የሚወሰነዉ በቀዳሚነት በምንሰጥበት የእምነት መጠንና በበጎ ርኅራኄያችን ላይ እንጂ በምንሰጠዉ የገንዘብ መጠን አይደለም፡፡ እነደዚህ ቢሆን ኖሮ ጽድቅ ምንም ምግባር ሃይማኖት ለሌላቸዉ ባለጸጎች የተሸጠች በመሰለን ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ምጽዋት መስጠትና መቀበል ነዉ ብለናልና የሰጠ ሁሉ ሳይቀበል አይቀርም፡፡ ‹‹ለሌሎች ዕረፍት ለእናንተም መከራ እንዲሆን አይደለም፣ ትክክል እንዲሆን ነዉ እንጂ፤ የእነርሱ ትርፍ ደግሞ የእናንተን ጉድለት እንዲሞላ በአሁኑ ጊዜ የእናንተ ትርፍ የእነርሱን ጉድለት ይሙላ››/2 ቆሮ 814/ ተብሎ እንደተጻፈ በዚህ እኛ ከመጸወትን በሰማይም በምድርም እንመጸወታለን፡፡ 
        
          ጌታም ዳግመኛ ሲመጣ የሚጠይቀን በዚህ ምድር ምን ሰጠህ ብሎ ነዉ፡፡/ማቴ 2533/ በዚህ የማይሰጥ በዚያ ከእግዚአብሔር ምንም በጎ ነገር ሊቀበል አይችልም፡፡ስለዚህ እንመጽዉት፤ ካለእርሱ የምንኖር አይደለንምና፡፡ ትልቁ የዓለማችን የተፈጥሮ ይልቁንም ለሰዉ ዘር እጅግ ጠቃሚዉ የሰላምና የማኅበረሰብ ሚዛን ምጽዋት ነዉ፡፡ እዉነተኛ የሀብት ማከፋፈያ መንገድ ቢኖርና ሰዎች ያለስግብግብነት ቢጠቀሙበት ኖሮ ይህ ሁሉ ጦርነት ለምን ይፈጠር ነበር? ምጽዋት ፍትሓዊ በሆነ መንገድ ዓለማቀፋዊ ሥርዓት ይዛ ስግብግብነትን ገትታ ተተግብራ ቢሆን ዓለም የጸጥታ ዋስትና ታገኝ ነበር፡፡
ከሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በረከት እና ረድኤት ያሳትፈን ፡፡
በሥጋችን ፤ በነፍሳችን እና በገንዘባችን ለፈጣሪያችን ተገዢ እንድንሆን የእግዚአብሔር ቸርነት ፤የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን - አሜን
                                              ከኢሚሬትስ - ዱባይ

ዋቢ
-      ሐመር መጽሔት
-      የዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የፌስቡክ ገጽ





9 comments:

  1. lib yalew lib yibel.joro yalew yisma...betam melkam timhirt new.Egzer yistilin...egnam yetechegeru wegenochachinin rediten yekibiru werashoch lemehon yabikan...ye kidus tomas berket yideribin..Amen!!

    ReplyDelete
  2. እግዚአብሔር ይስጥልን

    ReplyDelete
  3. Mastewalun adilon lenuro yemihon timihirt yadrgilin. GOD bless you more and more!!!

    ReplyDelete
  4. አሜን ከሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በረከት እና ረድኤት ያሳትፈን!!!

    ReplyDelete
  5. Kale Hiwot Yasemalen!

    ReplyDelete
  6. Dear Melaku Quale Hiywot Yasemalin
    May GOD bless u and ur family.

    ReplyDelete
  7. ዲያቆን መልአኩ
    ቃለ ሕይወት ያሰማልን።
    ዕውቀቱን ያብዛልህ።

    “እዉነተኛ የሀብት ማከፋፈያ መንገድ ቢኖርና ሰዎች ያለስግብግብነት ቢጠቀሙበት ኖሮ ይህ ሁሉ ጦርነት ለምን ይፈጠር ነበር? ምጽዋት ፍትሓዊ በሆነ መንገድ ዓለማቀፋዊ ሥርዓት ይዛ ስግብግብነትን ገትታ ተተግብራ ቢሆን ዓለም የጸጥታ ዋስትና ታገኝ ነበር፡፡”

    ወስብሐት ለእግዚአብሔር

    ReplyDelete