Sunday, January 1, 2012

ነገረ ልደቱ ለክርስቶስ



እንኳን ለብርሃነ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ
በገባው አምላካዊ ቃል መሠረት አዳምን ለማዳን የዘመናት መቆየት' የወር መጉደል ማለፍ' የቀናት መዛነፍ ሳይኖርበት፤ በቃሉ መሠረት በልበ ሥላሴ ታስባ በኖረች ጥንተ አብሶ (የቀደመ በደል) ካላገኛት፣ በንጽሕናና በቅድስና በድንግልናም ተጠብቃ ትኖር ከነበረችው፣ በሕሊና ሥላሴ የማይቆጠር ዕድሜ ካላት በሥጋ ግን 15 ዓመት ብላቴና ከሆነች ከንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ያለወንድ ዘር በብሥራተ ገብርኤል ተጸነሰ፡፡እንደ ሰው ሥርዓት 9 ወር 5 ቀን በኋላ ንጉስ ነኝ ብሎ ዙፋን ሳይዘረጋ፣ ቤተ መንግስት ሳያሠራ፣ ክቡር ነኝ ብሎ ወርቅ ሳይለብስ፣ ሰው በሚኖርበት ሳይሆን ከብቶች በሚኖሩበት በበረት ውስጥ በቤተልሔም አውራጃ ተወለደ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያንም ይህንን የጌታን ልደት ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት በመመደብ በድምቀት ታከብራዋለች፡፡ 


አምላክ ለምን ሥጋ ለበሰ? ለምን ተወለደ?
    ሰይጣን አስቀድሞ ከክብሩ በተዋረደበት ‹‹የአምላክነት ምኞት›› አዳምንም ፈትኖ ከገነት አስወጥቶታል፡፡ ሰይጣን አዳም ሲፈትን የእባብን አካል ተዋሕዶ በእባብ አካል አድሮ ነበር፡፡ አምላካችን ይህንን የሠይጣን ጥበብ ተመልክቶ አዳምን ለማዳን ሌላ ጥበብ አላስፈለገውም፡፡ ራሱ ሰይጣን በተጠቀመበት ጥበብ አዳምንና ዘሩን ሊያድን ሽቶ፤ ሰይጣን የእባብን አካል ተዋሕዶ አዳምን እንዳሳተ እግዚአብሔርም የሰውን ልጅ ሥጋ ተዋሕዶ አዳምን ለማዳን ሰው መሆን አስፈልጎታል፡፡
አዳም የፈለገውን የተመኘውን አምላክነት ሊሰጠው ሽቶ እግዚአብሔር የሰውን ሥጋ ለበሰ፡፡ በዘፍ.3. 22 ‹‹እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ›› የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ ሥጋ እንደሚለብስ የሚያጠይቅና በአንጻሩ ደግሞ የሰው ልጅ መልካሙንና ክፉውን ለመለየት የሚቻለው አምላክ መሆኑን ያሳያል፡፡
የተነገረውን ትንቢት ለመፈፀም   በኢሳ. 9.6 ‹‹ ህጻን ተወልዶልናል ወንድ ልጅም ተሰጥቶናል አለቅነትም በጫንቃው ላይ ነው ስሙም ድንቅ መካር ኃያል አምላክ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል ›› ያለው በተመሳሳይ እነሆ ድንግል ትጸንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም ዐማኑኤል ብላ ትጠራዋለች ›› (ኢሳ. 7.14) ተብሎ የተነገረው እንዲሁም በነቢዩ ዳዊት‹‹እነሆ በኤፍራታ ሰማነው በዱር ውስጥም አገኘ ነው ›› በማለት የተናገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ አምላክ በድንግል ማኅጸን አድሮ በጠባቡ የሰው አካል ተወስኖ እንደ ሰው ሥርዓት በቤተልሔም ተወለደ፡፡ ከቦታዎችም መርጦ በቤተልሔም መወለዱ አስቀድሞ በነቢዩ ሚኪያስ ‹‹አንቺ ቤተልሔም ኤፍራታ ሆይ አንቺ በይሁዳ ካሉት መካከል ትሆኝ ዘንድ ታናሽ ነሽ ከአንቺ ግን አወጣጡ አስቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ በእስራኤልም ላይ ገዢ የሚሆን ይወጣልኛል ›› (ሚኪ.5.2) ተብሎ የተነገረ ትንቢት ስላለ ነው፡፡
 
አምላክ ለምን ያለ ወንድ ዘር ተወለደ;
   
እግዚአብሔር ሔዋንን ሲፈጥራት ከአዳም ጎን ነበር ያስገኛት በመሆኑም ወንዶች እኛ ያለ ሴት እናንተን ሴቶችን አስገኝተናል እናንተ ግን ያለ ወንድ ልታስገኙን አትችሉም ብለው ይመኩ ነበርና ይህንን ትምክህት ለማራቅ እመቤታችን ያለ ወንድ ዘር እርሱን በፈቃዱ አስገኝታዋለች፡፡
   
2 ሳሙ.7.14  ላይ ‹‹ እኔም አባት እሆነዋለሁ እርሱ ልጅ ይሆንልኛል ››  ተብሎ እንደተጻፈ ለጌታችን ከአብ በቀር አባት የሚስፈልገው አይደለምና እንደ ሰው ሥርዓት እርሱን በመውለድ አባት የሚሆነው አያሻውምና ከድንግል ያለ ዘር ተወለደ፡፡
    ‹‹
ልደት ቀዳማዊ ተዐውቀ በደኃራዊ ልደት›› ‹‹ያለ እናት ቅድመ ዓለም የተወለደው ልደት፤ በምድር  ያለ አባት በተወለደው ልደት ታወቀ ›› እንዲል ቀድሞ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ያለ እናት መወለዱን ሊገልጥልን ስለ ወደደ ከእመቤታችን ያለ አባት ተወለደ፡፡
 
እግዚአብሔር አዳምን ለማዳን ለምን ፈለገ;
     የመጀመሪያው ምክንያት የአዳም በንስሐ መመለስ ነው እግዚአብሔር የሠዎችን መጥፋት አይወድም ፤ ይልቁን በሐዘን ከስሕተታቸው የሚመለሱትን ይወዳል ያድናል፡፡ በኢዮ.2.12 ‹‹ ከሩቅም ሆነው ባዩት ጊዜ አላወቁትም፤ በታላቅ ድምፅም ጮኸው አለቀሱ፤ መጎናጸፊያቸውንም ቀደዱ፤ በራሳቸውም ላይ ትቢያ ነሰነሱ›› በማለት እንደተፃፈ፤ እንዲሁም በወንጌል ‹‹ ይህ ልጄ ሞቶ ነበር፤ አሁን ግን ሕያው ሆኖአልና ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልና ›› (ሉቃ. 16.24) ተብሎ እንደተጻፈው እግዚአብሔር የሰዎችን ከጥፋት መመለስ እንጂ ጥፋትን አይሻምና ነው፡፡
   
ሁለተኛው ደግሞ በደል ክፋት የአዳም ተፈጥሮ ወይም ባሕርይ አይደለምና ከባሕርይው ውጪ    የሆነውን ነገረ ሊያርቅለት (ሊያድነው) አምላክ ስላሰበ፣
   
ፍጠረኝ  ሳይለኝ  ፈጥሬዋለሁና መዳንም በፈለገበት ጊዜ ላድነው ይገባኛል ብሎ ከፍቅር የተነሣ  ሊያድነው ወደደ፡፡
ዓለምን የማዳን ጥበብ ዓለምን ከመፍጠር ጥበብ እንዴት ይበልጣል( ይረቃል) ?


       የአንበሳ ሥጋ መብላት፤ የአህያ ሣር መጋጥ፤ የበሬ መዋጋት የሚያስደንቅ አይደለም የተለመደ ነውና የሰው መሞት አያስደንቅም የሰው ማረግ  ግን ያስደንቃል፣ ያስደምማል እንግዳ ነገር ነውና፡፡ ፈጣሪ  ፍጥረታትን በተለያየ አኳኋን ቢፈጥር አያስደንቅም ምክንያቱም ፈጣሪ መፍጠር የሚቻለው ሁሉን ማድረግ የማይሳነው ነውና  እግዚአብሔር በአምላክነቱ ሁሉ ይቻለዋልና ሟች ፈራሽ በስባሽ የሆነ ሰው ደግሞ መራብ' መጠማቱ' መሞቱ የሚያስደንቅ አይደለም፡፡ ለእኛ የተለመደ የባሕርይ ገንዘባችን ነውና፡፡ ነገር ግን ሰውን የአምላክን ሥራ ሲሰራ ቢያዩት ያስደንቃል፣ ያስደምማል፡፡ 
ሰው በዘላለማዊው የእግዚአብሔር ዙፋን ሲገለጥ በየማነ አብ(በአብ ቀኝ) በዘባነ ኪሩብ(በኪሩብ ጀርባ) ሲቀመጥ ማየት ድንቅ ጥበብ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የማይሞተውን፤ ሞትም የማይስማማውን ሲሞት ማየት በአንደበት ከመግለጽ በላይ የሆነ ድንቅ ነገር ነውና እግዚአብሔር ሞትንና ሲዖልን ዲያቢሎስን በሥልጣኑ ሳይሆን በሞቱ ድል ይነሳ ዘንድ የአዳምን ሥጋ መልበስ መወለድ ነበረበት፤ ስለዚህም ነው ‹‹ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ሰው ሆኖ ዓለምን ያዳነበት ጥበብ ይበልጣል›› የተባለው፡ 

አምላክ በመወለዱ(ሰው በመሆኑ) ምን ተጠቀምን?
  
ሰው አምላክ ሆነ፡- አምላክ ሰው በሆነ ጊዜ ሰው አምላክ ሆኗል፡፡ መለኮት ሥጋን ሲዋሐድ ረቂቁ  ገዘፈ ምሉዕ የሆነው መለኮት ተወሰነ፤ሥጋም መለኮትን ሲዋሐድ ግዙፉ ሥጋ ረቀቀ የተወሰነው (የተገደበው) ሥጋ ምሉዕ(በሁሉ ያለ) ሆነ ፍጡሩ አመስጋኙ ሥጋ ፈጣሪ የሚመሰገን ሆነ፡፡
ከዲያቢሎስ ቁራኝነት ተላቀቅን፡- ከአዳም በደል ጀምሮ ዲያቢሎስ የሚወለዱ ህጻናትን በእናታቸው ማኅጸን በዘር ምክንያት እየተቆራኘ ጥንተ አብሶ (የቀደመው በደል) ተብሎ ከልጅ ልጅ ሲተላለፍ የቆየውን የባርነት ቀንበር አምላክ ያለ ወንድ ዘር በመወለድ ይህንን የዲያብሎስ ቁራኝነት አራቀልን፡፡ ከሞት ከኩነኔ፤ ከፍዳ ከመርገም፤ ከሲኦል ከገሃነም፤ ከዲያቢሎስ ወጥመድ ከኃጢአት እኛ ልጆቹን አዳነን፡፡

አባት ብለን የምንጠራበት የልጅነት ሥልጣን ተሠጠን - ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም ›› ወይም የሥጋን ባሕርይ አምላክ ገንዘብ አድርጓልና እንደ ቀድሞው አርቀን ‹‹ፈጣሪያችን፤አምላካችን›› ብለን ሳይሆን የምንጠራው ‹‹አባታችን ›› ብለን አቅርበን እንጠራዋለን፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው ›› (ዮሐ.1.12) በማለት እንደተናገረ፡፡

  መምህረ ትሕትና ወፍቅር መድኃኔዓለም ከብርሃነ ልደቱ ረድኤት በረከት ያሳድርብን አሜን
                                         ወስብሐት ለእግዚአብሔር

11 comments:

  1. Amen! Kalehiwot yasemalin wendimachin....Egizabiher kante gar yhun!

    ReplyDelete
  2. kalehiwot yasemalin

    ReplyDelete
  3. enkuan abero aderesen
    mewsfin

    ReplyDelete
  4. where is your contact address?

    ReplyDelete
  5. kal hiwoten yasemalen

    ReplyDelete
  6. ዲያቆን
    እንኳን ለጌታችንና ለመደሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሰህ!
    እግዚእብሔር ረዥም እድሜ ይስጥህ።
    ቃሉን ለማስተምር ያትጋህ።

    ReplyDelete
  7. Kale hiwot yasemalen !

    ande teyake alege .....

    lemenden newe beza kulu alem belalibela thisas 29 yetekeberew ye geta lidete bezmene yhonnes thaias 28 eyehone? menem enkwan yekidus lalibela ledet be thahisas 29 bihonem? beza kulu alem yemibalewe legeta newe weyse le kedius lalibela? ebakeh Diacon melese betsetebe dese yelgale?

    ReplyDelete
  8. tshufochihin kechalk be pdf bihonu tiru new amaric yemayanebu computeroch silalu

    ReplyDelete
  9. ዲያቆን
    ቃለ ህይወት ያስማልን !!!
    ዕድሜ ይስጥልን ባባትህ እግር ተተክትህ የጌታ አገልጋይ እንድትሆን አምላክ ይርዳህ እመቤታችን ትጠብቅህ
    ድረ ገጹን ሳይ የተስማኝ ደስታ ፍጹም ልዩ ነው፡፡ በተለይ የእግዚአብሄር ቃል እንደ ማርና ወተት ከሚፈስባት ቅድስት ሃገር ኢትዩጵያ በረከቱ እንዳይጉልባት ህዝቡ በተለይ አለም አቀፍ ወረርሽኝ ለከበበው ወጣት ቃሉን ማደረስ ስራህ ነውና በርታ፡፡
    ጎንደር የቃሉ እውነት የገነባቸው አባቶች አሉና እነሱን ባንተ በኩል እናገኛለን የሚል ተስፋ አለኝ፡፡

    ReplyDelete
  10. ሰላም እንደምን ሰነበትክ ዲ.መልአኩ የምታዘጋጃቸው መልህክቶች በእውነቱ ስረሰሃተ ቤ/ክ ከመጠበቃቸውም በላይ ወቀወታዊ እና አስፈላጊ ናቸው የቤ/ክ አምለክ ጻጋውን ያብዛልህ ለዛሬው ነገረ ክርስቶስ የሚለውን ርህስ ቢቻል ሐለዋተ እግዚአብሔር ብትለው የአንድነት የሶአስትነትን ነገር እንዲሁም ከሶስቱ አካል አንዱ አካል የወልድን የባህሪ አምላክነት ለመግለጽም ሆነ ነገረ እግዚአብሄርን ለመግለጥ የሚአስችል ይሆናል እና ይህንን ለመጠቀም ብትሞከር መልካም ነው እላለው ታናሽ ወንድምህ

    ሰላመ እግዚአብሔር አይለይህ

    ReplyDelete