Wednesday, November 30, 2011

“ታቦተ ጽዮን” ፤ “ኅዳር ጽዮን“ ፤ “አክሱም ጽዮን “


 ክፍል -2

የቀዳማዊ ምኒልክ ጉዞና የታቦተ ጽዮን መምጣት
ቀዳማዊ ምኒልክ ከአደገ በኋላ በ12 ዓመቱ ከእናቱ የተሰጠውን ለታቦተ ጽዮንና ለንጉሥ ሰሎሞን እጅ መንሻ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ፡፡ ንግሥት ሳባም ለንጉሥ ሰሎሞን “ንጉሥ ሆይ ልጄን ሙሴ የጻፋቸውን ሕግጋት ሥርዓተ ክህነት አስተምረህ ላክልኝ፡፡” የሚል መልእክት ልካ ነበር፡፡ ቀዳማዊ ምኒልክ በኢየሩሳሌም ከአባቱ ዘንድ ለሦስት ዓመት ያህል ቆይቷል፡፡  በዚሁ ዘመን መጻሕፍተ ሙሴን፣ ሕገ መንግሥትን፣ ሥርዓተ ክህነትን የዕብራይስጥን ቋንቋ ከሊቀ ካህናቱ ከሳዶቅ ተምሯል፡፡
 ወደ ኢትዮጵያ ሲመለስም በፈቃደ እግዚአብሔር ታቦተ ጽዮንን ይዞልን መጥቷል፡፡ ይህች ታቦት ለ3000 ዓመታት ያህል እስከዛሬ ድረስ በኢትዮጵያ በአክሱም ትገኛለች፡፡ ንግሥት ሳባም ታቦተ ጽዮን መምጣቷን ስትሰማ ለእግዚአብሔር መስዋዕት አቀረበች፡፡ ሰዎችን መርጣ ታቦተ ጽዮንን እንዲጠብቁ አድርጋለች፡፡ የመንግሥቱን ሥልጣን በሙሉ ለቀዳማዊ ምኒልክ አስረክባ ከዚህ ዓለም በሞተ በተለየች ጊዜ በዚያው በአክሱም ተቀብራለች፡፡ ቦታውም እስከ አሁን ድረስ የንግሥት ሳባ መቃብር እየተባለ ይጠራል፡፡
በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረው ታሪክ ጸሐፊው አቡሳላህ “አቢሲኒያውያን በእግዚአብሔር ጣቶች አሥርቱ ቃለት የተጻፈባት፣ ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ያሉባት የቃል ኪዳኑ ታቦት አለቻቸው፡፡” በማለት ጽፎ ነበር፡፡ በዘመናችን ይህችን ታቦት ፍለጋ ያደረገው ግርሃም ሐንኮክም   “The sign and the seal” በተሰኘው መጽሐፉ ይህን ገልጦታል፡፡
ታቦተ ጽዮን በአክሱም


በኢትዮጵያ ታሪክ ልዩ ሥፍራ ከያዙት ቦታዎች ግንባር ቀደምትዋ የአክሱም ከተማ ናት፡፡ አክሱም የኢትዮጵያ የታሪክና የሃይማኖት እናት ከተማ ስትሆን ከክርስቶስ ልደት በፊት በ2ሺ ዓ.ዓ. እንደተቆረቆረች መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ አክሱም የቤተ ክህነቱም ሆነ የቤተ መንግሥቱ ማዕከል በመሆን ለብዙ ዘመናት አገልግላለች፡፡ በተለይም እግዚአብሔር ለሊቀ ነቢያተ ሙሴ የሰጠው የታቦተ ጽዮን  መንበር በመሆኗ ከተማዋን ድንቅ ሁኔታን ያጎናጽፋታል፡፡
በዘመነ ሐዲስም የክርስትና መዲና፣ የስብከተ ወንጌል ማዕከል ፤ የጳጳሳት መንበር ለመሆን መቻልዋም በቤተ ክርስቲያናችን የታሪክ ክፍል ውስጥ እንደ አጥቢያ ኮከብ እንድታበራ አድርጎአታል፡፡ የአክሱም ከተማ የ4000 ዓመት ዕድሜ ያላት ሲሆን ስለ ስያሜዋም ሊቃውንቱ ሲያትቱ፡-
1.       ከጌታችን ልደት በፊት 2000 ዓመት ገደማ የነበረውና የኩሽ የልጅ ልጅ /የኖኅ የልጅ፣ልጅ/የሆነው አክሱማዊ ስሙን ለቆረቆሩት ከተማ ማውረሱ ይነገራል፡፡ ከተማውን በቆረቋሪው መሰየም የጥንት ሰዎች ባህል ነበር፡፡ ዘፍ. 10፡1-32
2.      “አክሱም” የሚለው ቃል ከሁለት ጥንታውያን ቋንቋዎች የተገኘ ነው፡፡ “አኩ” በአገውኛ ቋንቋ ውኃ ማለት ሲሆን “ሱም” ደግም ከሴም ቋንቋ ተወስዶአል፡፡ ትርጉሙም “ሹም” ማለት ነው፡፡
3.      በሰሜን አክሱም አንድ የውኃ ጉድጓድ አለ፡፡ እሱም “ማይሹም” ይባላል፡፡ የከተማዋ መጠሪያ ከዚህ የተወሰደ ሳይሆን እንዳልቀረ አንዳንድ ሰዎች ይናገራሉ፡፡
4.      የአክሱም /አኩሽም - በዕብራይስጥ/ - ጥንታዊት፣ ቀዳማዊት የነገደ ኩሽ መዲና፣ አህጉረ ኩሽ ማለት ነው፡፡
5.      ገድለ መርቆሬዎስ ደግሞ “መካነ ዕንቁ ማለት ነው” ይላል፡፡ ለዚህም “ወበእንተዝ ተሰምየ ስማ ለይእቲ አክሱም፣ እስመ ትርጓሜሃ ለአክሱም መካነ ስም ብሂል ዝውእቱ መካነ ዕንቁ፡፡”  እንዲል፡፡
የአክሱም ከተማ ታሪክ ይበልጥ እየገነነ የመጣው ከጌታችን  ልደት በፊት 1000 ዓመተ ገደማ ጀምሮ ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ዘመን ንግሥት ሳባ የሰሎሞንን ጥበብ ለመስማት ወደ ኢየሩሳሌም የተጓዘችበትና ልጇ ቀዳማዊ ምኒልክ ታቦተ ጽዮንን በጥበበ እግዚአብሔር ወደ ኢትዮጵያ ያመጣበት ዘመን በመሆኑ ነው፡፡
የጽዮን በዓል አከባበር

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ኅዳር 21 ቀን  በታላቅ ክብር ታከብረዋለች፡፡ በዚሁ ዕለት የእመቤታችን ወዳጆች ምእመናን በዓሉን ለማክበርና ለመሳለም ወደ አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን በብዛት ይገሠግሳሉ፡፡ ዕጣን፡ ጧፍ፡ ዘቢብ መባውን ይሰጣሉ፡፡ ካህናቱም ከዋዜማው ጀምረው በከበሮና በጸናጽል ስብሐተ እግዚአብሔር ያደርሳሉ፡፡ በድርሳነ ጽዮን መጽሐፍ ካህናቱ እንደተገለጠው በጽዮን ፊት እንደየመዓርጋቸው ቆመው  “እግትዋ ለጽዮን ወህቅፍዋ” የሚለውን መዝሙር ከዳዊት እያወጣጡ ይጸልያሉ፡ ይዘምራሉ፡፡ ፈጣሪያቸውን እያመሰገኑ የታቦተ ጽዮንን ተራዳኢነት በምእመናን ፊት ይመሰክራሉ፡፡
 
ነቢያት ክርስቶስ ወዲዚህ ዓለም በሥጋ ማርያም ከመገለጡ በፊት ከእግዚአብሔር ተልከው ሕዝቡን ከአምልኮተ ጣዖት ከገቢረ ኃጢአት እንዲጠበቅ የሚመክሩ የሚያስተምሩና የሚያጽናኑ ነበሩ፡፡ ሉቃ 16፤17፣ ኢሳ. 40፤1፣ ኢሳ. 44፤1-11፡፡ የነቢያት ትንቢት ዋናው ዓላማ እግዚአብሔር አምላክ ሕዝቡን እንደተዋቸው እንደማይቀር፣ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሰው ሆኖ ተገልጦ ወንጌልን አስተምሮ ስለእኛ መከራን ተቀብሎ እንደሚያድነን መግለጥ ነበር፡፡ ኢሳ. 7፤14፣ ማቴ. 1፤ 23፣ ሚክ. 5፤2፡፡
ነቢያት ሁሉ ስለ ክርስቶስ በተለያየ ኅብረት ትንቢትና አምሳል እንደ ተናገሩ ሁሉ ክርስቶስ ስለሚገኝባት አማናዊት ድንግል ማርያምም ተናግረዋል፡፡ ስለ ክርስቶስ በትንቢትና በተምሳሌት የተናገሩ ሁሉ ስለርሷ ተናግረዋል፡፡

ኅዳር 21 ቀን የሚከበረውም የእመቤታችን ምሳሌዎች የተገለጡበት እና የተለያዩ ሥራዎች የተሰሩበት ዕለት ስለሆነ ነው፡፡ እነዚህም፡-
1.     ነቢዩ ዘካርያስ ሁለንተናው ወርቅ የሆነ፣ የዘይት ማሰሮ በራሱ ላይ የነበረበትንና ሰባት መብራቶች ያሉትን መቅረዝ ሲያበራ ያየበት ዕለት ነው፡፡ ዘካ. 4፤1-2፡፡ ዘካርያስ ያየው ብርሃን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዮሐ. 8፤12፡፡ ይህ ብርሃን የታየባትና የተገለጠባት መቅረዝ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት፡፡ ብርሃን መቅረዝ እንዲያዝና እንዲገለጥ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ተገልጦልናል፡፡ ጨለማ ዓለምን አብርቷል፡፡ ብርሃን ክርስቶስን ወልዳለችና እርሷም እመ ብርሃን / የብርሃን እናት/ ትባላለች፡፡
2.     ታቦተ ጽዮን ዳጎንን ገልብጣ በመጣል ኃይሏን የገለጠችበት ዕለት ነው፡፡ በፍልስጥኤማውያን ተማርካ ቤተ ጣዖት ወስደው ከጣዖታቸው ከዳጎን በታች አስቀምጠዋት ነበር፡፡ ታቦተ ጽዮን ግን በላይዋ ያለውን ዳጎንን ገልብጣ ጥላ እርሷ ከላይ ተቀመጠች፡፡ በታቦት የሚገለጠው የእግዚአብሔር ኃይል ነው፡፡ ምክንያቱም በታቦቱ ላይ ያለው ሕገ እግዚአብሔርና ስመ እግዚአብሔር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ስም የጸና ክንድ ነውና ሁሉን ያሸንፋል፡፡ ስለዚህ ምንም እንኳ ለጊዜው ስትማረክ ደካማ ብትመስልም መማረኳ  ግን ኃይሏን ለመግለጥ፣ ለአሕዛብ የጣዖትን ከንቱነት የታቦትን ክቡርነት ለመግለጥ ነበር፡፡ 
3.    ቀዳማዊ ምኒልክ ታቦቱን ይዞ አክሱም የገባበት፣ ንግሥት ሳባ ታላቅ በዓል አድርጋ የተቀበለችበት፣
4.    አብረሃ ወአጽብሐ በአክሱም ከተማ 12 ቤተ መቅደስ ያለው ቤተ ክርስቲያን በአስደናቂ ሁኔታ ሠርተው ከጨረሱ በኋላ ቅዳሴ ቤቱን ያከበሩበት፣ እንዲሁም
5.    በ9ኛው መ/ክ/ዘመን ዮዲት ክርስትና ለማጥፋት በተነሳች ጊዜ በእርሷ ምክንያት ታቦተ ጽዮን ወደ ዝዋይ ሐይቅ የተሰደደችበት፡፡ በኋላም የሰላሙ ዘመን ሲመጣ ተመልሳ አክሱም የገባችበት በዚሁ በኅዳር 21 ስለሆነ በእነዚህ በተደራራቢ ታሪኮች ምክንያት በየዓመቱ በደመቀ ሁኔታ ይከበራል “ኅዳር ጽዮን በአክሱም ጽዮን” የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡

ታቦተ  ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት፡፡

ሀ.    ታቦተ ጽዮን በወርቅ የተለበጠች ናት፡፡ ይህም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በነፍስ በሥጋዋ ንጽሕት የመሆንዋ ምሳሌ ነው፡፡ ወርቅ የንጽሕና የቅድስና ምሳሌ ነው፡፡ ሰብአ ሰገል ካመጡት እጅ መንሻ አንዱ ወርቅ ነው፡፡ ይኸውም የክርስቶስ ንጹሐ ባሕርይነት የሚገልጥ ነው፡፡
ለ.      እስራኤላውያን በምድረ በዳ 40  ዓመት መና መግቧቸዋልና ይህን ለሚመጣ ትውልድ በታቦቱ ዘንድ እነዲያስቀምጡ ታዘው ነበር፡፡ አንድ ጎሞር መና በታቦቱ ፊት አሮን አስቀመጠ፡፡ ዘጸ. 16፤31-34፡፡ እስራኤላውያን የተመገቡት መና የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዮሐ. 6፤58፡፡ መናው የተቀመጠበት ጽላተ ኪዳን ደግሞ አማናዊ መና ኢየሱስ ክርስቶስን በድንግልና ጸንሳ በድንግልና የወለደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡
ሐ.     በጽላቱ ላይ በእግዚአብሔር ጣት 10ቱ ቃላት ተጽፈዋል፡፡ ጽላቱ የእምቤታችን ምሳሌ ነው፡፡ በጽላቱ ላይ የተጻፈው ቃሉ የሥግው ቃል የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዮሐንስ በመጀመሪያ ቃል ነበር፡፡ ዮሐ. 1፤1 እንዳለ፡፡ በጽላቱ ላይ በአጻብአ እግዚአብሔር የተጻፈው ቃል ቃለ እግዚአብሔር ከእመቤታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ ነሥቶ ሕዋሳቶቿን ሕዋሳቱ አካሏን አካሉ አድርጎ ሰው የመሆኑ ምሳሌ ነበር፡፡

በአጠቃላይ ታቦተ ጽዮን ዳጎንን መቀጥቀጧና በክብር መመለሷ እመቤታችንም በእናቷ በሐና ማኅፀን ሳለች ጀምሮ የተነሱባትን  ጠላቶቿን አይሁድ አጋንንትን በኃይለ እግዚአብሔር ድል አድርጋ የአምላክ እናት ለመሆን ለመብቃቷና ከርሷ የሚገኘው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አጋንንትን ድል አድርጎ ግእዛነን እንደሚመልስልን፣ ከሲዖል ነፃ እንደሚያወጣንና በክብር ወደ ቀደመ ክብሩ ወደ ጥንት አኗኗሩ እንደሚያደርግ የገለጠና ያስረዳ ተምሳሌት ነበር፡፡
ታቦተ ጽዮን በእግዚአብሔር ፈቃድ በቀዳማዊ ምኒልክ ወደ ኢትዮጵያ ገብታ በአክሱም ከተቀመጠችበት ጊዜ ጀምሮ ሀገራችን በረከት፣ ረድኤት ሳይለያት በየዘመኑ የተነሱ ጠላቶችን ድል እያደረገች መልሳለች፡፡ እግዚአብሔር በታቦተ ጽዮን ላይ በረድኤት እያደረ የሕዝቡን ችግር እንዳስወገደ ሁሉ ዛሬም ችግራችንን እንዲያቃልልን፣ በረድኤት እንዲጎበኘን ዘወትር በጸሎት ታቦተ ጽዮንን ልንማጸን ይገባል፡፡ ለእስራኤላውያን በታቦቱ ላይ እያደረ እየተገለጠ ያናገረ የባረከ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር አይለየን፡፡

ጽዮን የተባለች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጣዕመ ውዳሴዋ ሀብተ ረድኤቷ በሁላችን ላይ አድሮብን ይኑር፡፡ ለዘላለሙ አሜን፡፡
በዓሉን በዓለ ፍስሐ በዓለ ደስታ ያድርግልን

17 comments:

  1. Amen !
    kale Hiwote yasemalene yeaglegelote zemnkene yarzemelene.

    Kumilachew M.

    ReplyDelete
  2. Mele bewunetu rejim edime na tena yisitilin!!!!!!!!!!!!!!!

    ReplyDelete
  3. Egziabhere Yibarkih!

    ReplyDelete
  4. kale hiwot yasemalen Egziabher yagelegilot zemenken yibarikleh

    ReplyDelete
  5. amen kale hiwot yasemalen. Egziabher amlak yagelegilot zemenken yibarikleh.edmen ketena aynsah.

    ReplyDelete
  6. Amlake Kidus Lalibela yibarkih! Kale hiwot yasemalin endante ewnet ewnetun eminager sew yabizalin! Ethiopia tabetsh edweiha habe egizabher!

    ReplyDelete
  7. kale hiwot yasemalin

    ReplyDelete
  8. Kale hiwotin yasemalin. Legnam texmiratuana berketua hagerachinina hizbachinin kekifu mekerana mesenakil yitebikilin zend Y leoul Egziabher fekadu yihunilin!

    ReplyDelete
  9. እግዚአብሔር ይስጥልን የአገልግሎት ዘመንህ ይባረክ ንግሥት ሳባ እና ማክዳ ይምታቱብኝ ነበር ግልጽ አድርገን ስለጻፍከው ደስ ብሎኛል፡፡

    ReplyDelete
  10. ye emebetachin amalajinet ke hagerachin ETHIOPIA ayiley AMEN

    ReplyDelete
  11. kalehiwot yasemalen tesfa mengiste semayatn yawrselen

    welete michael

    ReplyDelete
  12. ቃለ ሒወት ያሰማለን፡፡ እግዚአብሔር የአገልግሎተ ግዚህን ይባርክለክ፡፡ አሜን፡፡

    ReplyDelete
  13. እግዚአብሔር አግልግሎትን ያስፋልን ሁሌም በንጹህ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ለመበረዝ ያላቸውን ክፉ ሃሳብ አመላክ ሃሳባቸውን ያጥፋልን ፡፡ አንተንም እግዚአብሄር እድሜና ጤናን ያድልልን፡፡

    ReplyDelete