Monday, November 28, 2011

“ታቦተ ጽዮን” ፤ “ኅዳር ጽዮን“ ፤ “አክሱም ጽዮን “ ክፍል -1



       የታቦተ ጽዮን መንበር -አክሱም

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓላት አንዱ “ኅዳር ጽዮን” ሲሆን የሚከበረውም ኅዳር 21 ቀን ነው፡፡ የበዓሉን አከባበር ፤ ጥንተ ታሪኩን፤ ንግስት ሳባ ፤ቀዳማዊ ምኒልክና ሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮችን በተከታታይ ክፍሎች እንመለከታለን፡፡ 
ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  “ታቦተ ጽዮን” የፈጸመችውን ልዩ ልዩ ተአምራት ለምእመናን እያስተማረች በታላቅ ድምቀት የምታከብረው ቅዱሳት መጻሕፍትን መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ በደብረ ሲና አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከጾመና ከጸለየ በኋላ ዐሥርቱ ቃላተ የተጻፈበትን ጽላት /ታቦተ ጽዮን/ ከእግዚአብሔር እጅ ተቀበለ፡፡  “ታቦተ ጽዮን” የሚለውንም ስያሜ ያገኘችው ጽዮን ተብላ በምትጠራው የእስራኤል ከተማ ስም ነው፡፡ ጽዮን ማለት ተፀወነ፡- ተጠጋ፣ ተማጠነ ማለት ነው፡፡ ክቡረ ዳዊትም ጽዮንን አምባ፣ መጠጊያ አድርጎ ብዙ ጠላቶቹን ተዋግቶ አሸንፎ ድልን ተጎናጽፏል፡፡

አጼ ፋሲል በ16ኛው ክፍለዘመን ያሰሩት ቤተክርስቲያን ከፊት ለፊት እና በጎን ሲታይ
ጽዮን የተባለችው የታላቁ የዳዊት ከተማ የተገፉና የተበደሉ ሕዝቦች ሁሉ እውነተኛ ፍርድ ለማግኘት፣ ተሰብስበው የሚሰነብቱባት ከተማ ስለነበረች፣ ጽላተ ሙሴም በዚያ ስለነበረች በርሷ ተማጽነውም ችግራቸው ሰለሚቃለል ታቦቷ “ታቦተ ጽዮን” ተብላለች፡፡
ዮሐንስ ፍቁረ እግዚእ በራእዩ “በሰማይ ያለችው የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ተከፈተች፡፡ በውስጧም ያለችው ታቦተ ሕግ ታየች፡፡” ራእይ. 11 ሚ 19 በማለት የተናገረውን ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በመጽሐፈ አክሲማሮስ ሲተረጉመው “በሥላሴ ጸዲል በሥላሴ ብርሃን የተመላች ስመ ሥላሴ የተጻፈባት ታቦት በኢየሩሳሌም ሰማያዊት አለች፡፡ በዚህች ታቦት ላይ ከፍጥረተ ዓለም በፊት ስመ እግዝእትነ ማርያም ተጽፎባት ነበር፡፡ ቅድመ ዓለም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከመፈጠሯ በፊት በአምላክ ኅሊና ታስባ ትኖረ ነበር የሚለው መሠረቱ ይህ ነው” ብሏል፡፡ ታቦተ ጽዮን የምትኖርበትን ድንኳን ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንዲሠራ እግዚአብሔር ነግሮታል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ሲናገር “ደብተራ ኦሪትን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት አርአያና ምሳሌ እንዲሠራ እግዚአብሔር አሳይቶታል፡፡ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ሁለንተናዋ ከብርሃን የተሠራች ናት፡፡ የኢየሩሳሌም ሰማያዊት ቅርጽም ደብተራ ኦሪትን ትመስላለች፡፡” ይላል፡፡ ሕዝቡም ከፈጣሪያቸው ጋር ቃል ኪዳን ገብተው በታቦተ ጽዮን አማካኝነት ሲያመሰግኑ ኑረዋል፡፡
ታቦተ ጽዮን እግዚአብሔርን ለሚያምኑ፣ ሕጉን ትእዛዙን ለሚፈጽሙ ሰዎች ሁሉ ልዩ ልዩ ተአምራትን እንደፈጸመች ከቅዱስ መጽሐፈ እንረዳለን፡፡ እስራኤላውያን ሕጉን ሲጠብቁ ትእዛዙን ሲፈጽሙ እግዚአብሔር በታቦተ ጽዮን እያደረ ይረዳቸውና ጠላቶቻቸውንም ድል ያደርጉ ነበር፡፡ ሕጉን ሲያፈርሱ ደግሞ በጠላቶቻቸው ይሸነፉ ነበር፡፡
አጼ ኃይለሥላሴ ያሰሩት ቤተክርስቲያን - አክሱም
በዚያ ዘመን ኤሊ የሚባል ሊቀ ካህናት ነበር፡፡ አፍኒንና ፊንሐስ የሚባሉ ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ እድሜውም 98 ዓመት ነበር፡፡ አፍኒንና ፊንሐስ የአባታቸውን ምክር አቃልለው የማይገባ ኃጢአት ሠርተው አምላካቸው እግዚአብሔርን አሳዘኑ በራሳቸው ፈቃድ ተጉዘው ሕገ እግዚአብሔርን ጣሱ፡፡ በሕዝቡም ላይ የሚያደርሱት በደል እየጨመረ ሔደ፡፡
አፍኒንና ፈንሐስ እግዚአብሔር በኃጢአታቸው ምክንያት በረድኤት ስለተለያቸው ፍልስጥኤማውያን በጠላትነት ተነሡባቸው፡፡ እስራኤላውያን ከኤሊ ልጆቸ ጋር ሆነው በአንድነት ታቦተ ጽዮንን ይዘው ለጦርነት ወደ ፍልስጥኤም ዘመቱ፡፡ ጦርነትም ገጠሙ ታላቅ ግድያም ሆነ፡፡ በጦርነቱ አፍኒንና ፊንሐስ ሞቱ፡፡ ታቦተ ጽዮንም በኤሎፍላውያን እጅ ተማረከች፡፡ ሕዝቡም በጦርነት አለቁ፡፡ ከጦርነቱ ያመለጠ አንድ ሰው ወደ ኤሊ ሄዶ እስራኤላውያን ተሸንፈው መሸሻቸውን፡ ሁለቱ ልጆቹ አፍኒንና ፊንሐስ መሞታቸውን ታቦተ ጽዮንም መማረኳን ነገረው፡፡
ኤሎፍላውያንም ታቦተ ጽዮንን ማርከው ከወሰዷት በኋላ ዳጎን ከተባለው ጣዖታቸው በታች አስቀመጧት፡፡ በማግስቱ የዳጎን አገልጋዮች መጥተው ቢያዩአት ፣ ዳጎን ከእግዚአብሔር ታቦት ፊት በግንባሩ ተደፍቶ አገኙት፡፡ አንስተው አቁመውት ሔዱና በማግስቱ መጥተው ቢያዩት በግንባሩ ወድቆ እጆቹ ተለያይተው ጣቶቹም ተቆራርጠው ደቀው በወለሉ ላይ ተበታትነው ነበር፡፡ ታቦተ ጽዮን ግን ምን ጉዳት ሳይደርስባት ከላይ ሆና አገኙአት፡፡ አገልጋዮቹም ታቦተ ጽዮን ያደረገችውን ተአምር በማድነቅ ዳጎንን በመናቅና በማቃለል ከዚያ ቀን ጀምረው ከቦታው ፈጽመው አልደረሱም፡፡ 1ኛ ሳሙ 5፤1-7፡፡ ሕዝቡም በሰውነታቸው ላይ እባጭ እየወጣባቸው ሲገድላቸው ሌሎቹንም በሚያንቀጠቅጥና በሚጥል በሽታ እያሰቃያቸው፣ እህላቸው በአይጥ፣ እንስሶቻቸው በበሽታ አለቁባቸው፡፡
ታቦተ ጽዮን በኤሎፍላውያን ላይ እንዲህ ያለ ተአምር እየፈጸመች በፍልስጥኤም አገር ለሰባት ወራት ቆይታለች፡፡ ከሰባት ወራት በኋላ ኤሎፍላውያን ታቦተ ጽዮንን ወደ ሀገሯ ለመመለስ ወርቅ በሳጥን አድርገው በሠረገላ ጭነው በላሞች እያስጎተቱ ወደ ሀገሯ ሰደዷት፡፡ እስራኤላውያን የታቦተ ጽዮንን መመለስ በሰሙ ጊዜ በዕልልታ በሆታና በዝማሬ ተቀብለው አሚናዳብ ቤት አስገቧት፡፡ በዚያም ሃያ ዓመታት ኑራለች፡፡ የአሚናዳብ ቤት በታቦተ ጽዮን ምክንያት ተባርኮለታል፡፡ 1ኛ ሳ. 7፤2፡፡
ንጉሥ ዳዊት ታቦተ ጽዮን ወደ ከተማው በመጣች ጊዜ ከዙፋኑ ተነስቶ እየዘመረ በክብርና በምስጋና ተቀብሏታል፡፡ ብዙ መስዋዕትም ተሰውቷል፡፡ 2ኛ ሳሙ 6፤14፡፡ ታቦተ ጽዮን እስከ ንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ድረስ በድንኳን /በደብተራ ኦሪት/ ከተቀመጠች በኋላ በንጉሡ ሰሎሞን በተሠራው ቤተ መቅደስ ገብታለች፡፡ 1ኛ ነገ. 8፤1-12፡፡
የንግሥተ ሳባ ጉዞ ወደ ኢየሩሳሌም
ከጌታችን ልደት በፊት በ1ሺ ዓ.ዓ. በኢትዮጵያ የነገሠችው ንግሥት ሳባ ሦስት ስም አላት፡፡ በመጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ ምዕራፍ 10፤1-10 እና በ2ኛ ዜና 9፤1-8 ላይ “ሳባ” በማለት ትጠራለች፡፡ በክብረ ነገሥት ደግሞ  “ማክዳ” ተብላለች፡፡ ጌታችን በመዋዕለ ትምህርቱ “ንግሥት አዜብ” ብሏታል፡፡ ማቴ 12፤42፡፡ አዜብ ማለት ደቡብ ማለት ሲሆን ኢትዮጵያ በድሮ ግዛትዋ ለእስራኤል ደቡብ ነበረች፡፡ ጌታ ንግሥት አዜብ ያላትም ለዚህ ነበር፡፡ ይህንን ቃል ከእርሷ በኋላ 1500 ዓመት ቆይተው የተነሱት የኢትዮጵያ ነገሥታት ሳይቀሩ ይጠቀሙበት እንደነበር የቤተ ክርስቲያን መዛግብት ያስረዳሉ፡፡
ስለ ንግሥት ሳባ ኢትዮጵያነት የሚያስረዱ የተለያዩ ማስረጃዎች ይገኛሉ፡፡ ከጥንታውያን የታሪክ ጸሐፍት መካከል የሚቆጠረው ዮሴፍ ወልደ ኮርዮን ስለዚህችው ንግሥት “በዚያን ጊዜ የኢትዮጵያና የግብጽ ንግሥት የነበረችው” በማለት ነበር የጻፈው፡፡ ላዕላይ ግብጽ ከጥንት ጀምሮ የኢትዮጵያ ግዛት እንደነበር የታወቀ ነው፡፡ የግብጻውያን ትልቁ የታሪክ መዝገብ የሆነው የፓትርያርኮች ታሪክም እንዲህ ይላል “የታላቁ ሀገር አቢሲኒያ ንግሥት እርስዋም ንግሥት ሳባ የምትባል የደቡብ ንግሥት፣ ወደ ዳዊት ልጅ ሰሎሞን መጣች፡፡” ይላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም  በኢትዮጵያችን ከንግሥት ሳባ ጋር የተያያዙ ልዩ ልዩ የአርኪዎሎጂ /የከርሰ ምድር ጥናት/  ውጤቶች ተገኝተዋል፡፡
የንግስት ሳባ ቤተመንግሥት በአርኪዎሎጂ የተገኘ - አክሱም
የንግሥተ ሳባ ትውልድ ቦታ፡- በሰሜን ደንገሎ፣ በደቡብ ፎካደ በተባሉ በሁለት ተራሮች መካከል የሚገኝ ሲሆን ስሙም  “ጎሎ ማክዳ” ይባላል፡፡
የንጉሥ ምኒልክ አንደኛ መቃብር፡- አክሱም ከተማ በስተምዕራብ 2 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ በ1906 የደች ልዑካን የአርኪዎሎጂ ጥናት በሚያደርጉበት ወቅት ከምድር ውስጥ የተቀበረ ቤት ውስጥ የንጉሥ ምኒልክን ዐጽም ያገኙ ሲሆን የአክሱም ጽዮን ካህናት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በክብር እንዳሳረፉት ይታወቃል፡፡
በ13ኛው መ/ክ/ዘመን የነበሩት የአክሱም ንቡረ ዕድ ይስሐቅ ከተለያዩ ምንጮች ክብረነገሥትን ሲያዘጋጁ እጅግ ታላቅ ቦታ ከሰጡዋቸው ታሪኮች መሐል አንዱ የንግሥት ሳባ ታሪክ ነው፡፡ ንግሥት ሳባ እግዚአብሔርን በመፍራት በመልካም ሁኔታ ሕዝቡን ታስተዳድር ነበር፡፡ በወቅቱ በእስራኤል ላይ ነግሦ የነበረውን የሰሎሞንን ጥበብ በጆሮ መስማት ብቻ በቂ ሆኖ ስላላገኘችው በዓይን አይቶ መረዳት የበለጠ መሆኑን ተገነዘበች፡፡
ለንግሥት ሳባ ወደ ኢየሩሳሌም መጓዝ ምክንያት የሆናት ታምሪን የተባለው ነጋዴ ነው፡፡ ይህ ነጋዴ በኢየሩሳሌም በሚቆይበት ጊዜያት ብዙውን  ጊዜ የሚያሳልፈው የሰሎሞንን ሥጋዊና መንፈሳዊ ጥበብ በማየት ነው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ በሚመለስበትም ጊዜ እየዘረዘረ ለንግሥት ሳባ ይነግራትና ያስረዳት ስለነበር፤ ንግሥት ሳባ ከዚሁ ነጋዴ በሰማችው ዜና የንጉሥ ሰሎሞንን ጥበብ ለማየት ጓጓች፡፡ በዚህም የተነሣ በታምሪን መሪነት ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ እግዚአብሔርም መንገዱን አቀናላት፤ ያለአንዳች መሰናክል ተጉዛ ኢየሩሳሌም ደረሰች፡፡ ለታቦተ ጽዮን ክብርና ለንጉሥ ሰሎሞንም ገጸ በረከት አቀረበች፡፡ 1ኛ ነገ. 10 ሚ 1-13፡፡
ንጉሥ ሰሎሞንም እርሷንና ተከታዮቿን በጥሩ መስተንግዶ ተቀበላቸው፡፡ ንግሥት ሳባም የቤተ መንግሥቱን ሥርዓትና ሥጋዊና መንፈሳዊ ጥበቡን ቀሰመች፡፡ በኢየሩሳሌም ቆይታዋ ከንጉሡ ቀዳማዊ ምኒልክን ፀነሰች፡፡ ወደ ኢትዮጵያም ተመልሳ ልጇን ምኒልክን በዛሬዋ አሥመራ ከተማ አጠገብ እንደወለደችው ይነገራል፡፡
ይቆየን - ቀጣዩን በሚቀጥለው ክፍል
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ዋቢ
-      መጽሐፍ ቅዱስ
-      ሐመር መጽሔት
-      ነቅዓ ጥበብ ዘፈለገ ሕይወት
-      የአክሱም ታሪክ

18 comments:

  1. thank you Diacon Melaku! may God bless your work!

    ReplyDelete
  2. kale hiwot yasemalen e/r yebarekehe

    ReplyDelete
  3. እግዚአብሄር በረከቱን ያብዛለህ፡፡ እየተከታተልን ነው፡፡ ነገር ግን ሰዉ የሚያወቀው እንዳይመስለው ርእስ ላይ አንዳንድ ልዩ ቃላቶች (በፅሁፉ ከተካተቱ) add አድርገህ ብትጽፈው፡፡

    ReplyDelete
  4. እግዚአብሄር ይባርክህ !!!!

    ReplyDelete
  5. kale hiwot yasemaln.egzabher tsegahn yabzalh

    ReplyDelete
  6. qale hiwoten yasemalen, እግዚአብሄር ይባርክህ !

    ReplyDelete
  7. kale hiwet yasemalen ye agelgelot zemenehen yebarkeleh!

    ReplyDelete
  8. ቃለ ህይወት ያሰማልን

    ReplyDelete
  9. Lehidar Enatachin Kidist Dingil Mariam Ametawi Kibre Behal Enquan Beselam Aderesachuh!

    ReplyDelete
  10. May God bless you abundantly! Remain blessed!

    ReplyDelete
  11. Egziabhere Yeagelgilot Zemenhen Yibarklih! Yemebetachin Amalajinet, Yetsadkan Semaetat Tselot, Yekdusan Melaekt Berket Ayleyeh Ayleyen, Yesemanewn/Yanebebnewn Belbonachen Yasadrben! Amen!

    ReplyDelete
  12. BETAM DES YILAL HONOM GIN AZEB MALET SEBUBAWI MISRAK WEYM MISRAK MESELEGN YIHENN BEMASREGA ASDEGFEH BITAKERBEW DES YILEGNAL

    ReplyDelete
  13. mele kalehiwet yasemalen eregem edmena tena yestelen

    ReplyDelete
  14. ቃለ ህይወት ያሰማልን

    ReplyDelete
  15. kalehiwot yasemalen tesfa mengiste semayat yawreselen

    welete michael

    ReplyDelete
  16. ቃለ ሕይወት ያሰማልን

    ReplyDelete